Popular Posts

Monday, December 4, 2017

በእግዚአብሄር ቃል የመኖር አምስቱ ደረጃዎች

በእውነት ፍሬያማ ለመሆን በክርስቶስ መኖር ግድ ነው፡፡ የፍሬያማነታችን ልክ በክርስቶስ የመኖራችን ልክ ብቻ ነው፡፡ በኢየሱስ መኖር ደግሞ በቃሉ መኖር ነው፡፡ በእግዚአብሄር ቃል የመኖር አምስቱን ደረጃዎች ከመፅሃፍ ቅዱስ አንመልከት፡፡
የእግዚአብሄርን ቃል መስማት
በቃል የመኖር የመጀመሪያው ደረጃ የእግዚአብሄርን ቃል መስማት ነው፡፡ ካለ እግዚአብሄር ቃል መስማት ፍሬያማነት የማይታሰብ ነው፡፡ የፍሬማነታችን ቁልፍ በቃሉ መኖር ነው፡፡ ስለዚህ ቃሉም ለመስማት ራሳችንን ልንሰጥ ይገባል፡፡ ቃሉን መስማት ሁኔታዎችን ማመቻቸት አለብን፡፡ በአሁኑ ጊዜ በተለይ በአሁኑ ጊዜ መፅሃፍ ቅዱስ በኰምፒተር በታብሌት በስልካችን በፅሁፍና በድምፅ እናገኘዋለን፡፡ በቤታችን ቴፕ ውስጥ ከፍተነው ማዳመጥ እንችላለን፡፡ መኪና ስንነዳና ወረፋ ስንጠብቅ ቃሉን መስማት እንችላለን፡፡  
እንግዲያስ እምነት ከመስማት ነው መስማትም በእግዚአብሔር ቃል ነው። ዕብራዊያን 10፡17
ለእግዚአብሄርን ቃል የመጀመሪያውን ስፍራ መስጠት
ፍሬያማ የሚያደርገን ቃሉ እንደመሆናችን መጠን ጠላትም የሚመጣው ቃሉን ሊነጥቅ ነው፡፡ ቃሉን ከሰረቀ ህይወታቸንነ ይሰረቃል ቃሉን ከጠበቅን ህይወታቸነ በደህንነት የጠበቃል፡፡ ሰይጣን ቃሉን ከሰረቀን ፍሬያችንን ሰረቀን፡፡ ሰይጣን ቃሉን መስረቅ ካልቻለ ምንም ነገራችንን መስረቅ አይችልም፡፡
የመንግሥትን ቃል ሰምቶ በማያስተውል ሁሉ፥ ክፉው ይመጣል፥ በልቡ የተዘራውንም ይነጥቃል፤ በመንገድ ዳር የተዘራው ይህ ነው። ማቴዎስ 13፡19
ሰው ውድ የሆነ ነገሩን እጅግ ውስጠኛው ቦታ ያስቀምጠዋል እንጂ ውጭ አይተወውም፡፡ እንዲሁ የእግዚአብሄርን ቃል የመጀመሪያውንም ስፍራ ልባችንን ልንሰጠው ይገባል፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል ለመሰረቅ በማይመች በውስጠኛው የህይወታችን ክፍል ውስጥ ልናደርገውና በልባችን ልንሰውረው እና ልንሸሽገው ይገባል፡፡  
ከእርሱም ይልቅ እጅግ የጸና የትንቢት ቃል አለን፤ ምድርም እስኪጠባ ድረስ የንጋትም ኮከብ በልባችሁ እስኪወጣ ድረስ፥ ሰው በጨለማ ስፍራ የሚበራን መብራት እንደሚጠነቀቅ ይህን ቃል እየጠነቀቃችሁ መልካም ታደርጋላችሁ። 2ኛ ጴጥሮስ 1፡19
በፍጹም ልቤ ፈለግሁህ፥ ከትእዛዝህ አታርቀኝ። አንተን እንዳልበድል፥ ቃልህን በልቤ ሰወርሁ። መዝሙር 119፡10-11
የእግዚአብሄርን ቃል ማሰላሰል
የእግዚአብሄርን ቃል ለመታተዘዝ ያስችለን ዘንድ በቃሉ ከባቢ ውስጥ ለመገኘት የእግዚአብሄርን ቃል ማሰብና ማሰላሰል ወሳኝ ነው፡፡ ቃሉን ስናሰላስል ቃሉን እናስታውሳለን፡፡ ቃሉን ስናሰላስል ቃሉን ለማድረግ ሃይል እናገኛለን፡፡
የዚህ ሕግ መጽሐፍ ከአፍህ አይለይ፥ ነገር ግን የተጻፈበትን ሁሉ ትጠብቅና ታደርግ ዘንድ በቀንም በሌሊትም አስበው፤ የዚያን ጊዜም መንገድህ ይቀናልሃል ይከናወንልሃልም። ኢያሱ 1፡8
በቀረውስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ እውነተኛ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ጭምትነት ያለበትን ነገር ሁሉ፥ ጽድቅ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ንጹሕ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ፍቅር ያለበትን ነገር ሁሉ፥ መልካም ወሬ ያለበትን ነገር ሁሉ፥ በጎነት ቢሆን ምስጋናም ቢሆን፥ እነዚህን አስቡ፤ ፊልጵስዩስ 4፡8
የእግዚአብሄርን ቃል መናገር
ሌላው የእግዚአብሄርን ቃል የምናደርግበት መንገድ የእግዚአብሄርን ቃል መናገር ነው፡፡ ንግግራችን እንደ እግዚአብሄር ቃል መሆን አለበት፡፡   
እውነት እላችኋለሁ፥ ማንም ያለው ነገር እንዲደረግለት ቢያምን በልቡ ሳይጠራጠር፥ ይህን ተራራ፦ ተነቅለህ ወደ ባሕር ተወርወር ቢል ይሆንለታል። ማርቆስ 11፡23
የእግዚአብሄርን ቃል ማድረግ
ነገር ግን ነጻ የሚያወጣውን ፍጹሙን ሕግ ተመልክቶ የሚጸናበት፥ ሥራንም የሚሠራ እንጂ ሰምቶ የሚረሳ ያልሆነው፥ በሥራው የተባረከ ይሆናል። ያዕቆብ 1፡25
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ፍሬያማነት #ፍሬ #ማፍራት #ስኬት #በእኔኑሩ #ቃል #ማሰላሰል #መጠበቅ #ማደርግ #መታዘዝ #መናገር #ስፍራመስጠት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #መመዘኛ #መስፈርት #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment