Popular Posts

Tuesday, December 19, 2017

አማኑኤል - እግዚአብሔር ከእኛ ጋር

እግዚአብሄር ሰውን ከእርሱ ጋር ፍፁም ህብረት እንዲያደርግ አድርጎ በመልኩና በአምሳሉ ፈጥሮታል፡፡ የእግዚአብሄር አላማ ከሰው ጋር በህብረት መኖር ነበር፡፡
ሰው ግን አታድርግ የተባለውን በማድረጉ በአመፅ ከእግዚአብሔር ተለየ፡፡ ሰው በእግዚአብሄር ላይ በማመፁ ምክኒያት ከእግዚአብሄር ጋር ተቆራረጠ በዚያም ከእግዚአብሄር ጋር የነበረውን የአባትና የልጅ ግንኙነት አጣው፡፡ ሰው ሰይጣንን በመስማቱ በአመፁ የእግዚአብሄር ጠላት ሆነ፡፡
እግዚአብሄር በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረው አንድም ሰው እንዲጠፋ አይፈልግም፡፡
ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው። 1 ጢሞቴዎስ 2፡3-4
ስለዚህ እግዚአብሄር ሰውን ለመፈለግ ስጋ ለብሶ ወረደ፡፡ ኢየሱስ በእግዚአብሄር መልክ ሲኖር እኛን ሰዎችን ለመፈለግ ስጋ ለብሶ ወደ ምድር መጣ፡፡
ልጅም ትወልዳለች፤ እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ። በነቢይ ከጌታ ዘንድ፦ እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ይሉታል የተባለው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሁሉ ሆኖአል፥ ትርጓሜውም፦ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር የሚል ነው። ማቴዎስ 1፡21-23
እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር አልቈጠረውም፥ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ፥ በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረደ፥ ለሞትም ይኸውም የመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ሆነ። ፊልጵስዩስ 2፡5-7
ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ ዮሃንስ 1፡14
ኢየሱስ እኛን ሰዎችን መስሎ የመጣው ለእኛ ያለውን ፍቅር ሊገልፅልንና ከሰው ጋረ የነበረውን የተበላሸ ህብረት ለማደስ የሚያስፈልገውን የሃጢያታችንን ዋጋ በመሞት ሊከፍልልን ነው፡፡
በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና። ዮሃንስ 3፡16
እግዚአብሄር በኢየሱስ በመካከላችን ቢያድርም ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሰራው ስራ ለእኔ ነው ብለን እስካልተቀበለን ድረስ ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣበትና የእኛን ስጋ ለብሶ የተመላለሰበትን ብሎም ስለሃጢያታችን የሞተበትን አላማ እንስተዋለን፡፡
ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤ ዮሃንስ 1፡12
ኢየሱስ ጌታ እንደ ሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው በልብህ ብታምን ትድናለህና፤ ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና። ሮሜ 10፡9-10
የንስሃ ፀሎት
እግዚአብሄር ሆይ ስለሃጢያቴ እንዲሞት ልጅህን ኢየሱስን ወደምድር ስለላከው አመሰግንሃለሁ፡፡ እግዚአብሄር ሆይ እኔ ሃጢያተኛ ነኝ፡፡ በሃጢያቴ ምክኒያት ለዘላለም ከአንተ መለየት አልፈልግም፡፡ እኔ ከአንት ለዘላለም እንዳልለያይ ኢየሱስ በመስቀል ላይ የሰራለኝን ስራ ለእኔ ነው ብዬ እቀበላለሁ፡፡ ኢየሱስ እንደሞተልኝና ከሙታን እንደተናሳ አምናለሁ፡፡ ኢየሱስ ጌታ እንደሆነ በአፌ እመሰክራለሁ፡፡ ኢየሱስ ጌታ ነው፡፡ ልጅ አድርገህ ስለተቀበልከኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ አሜን
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #መናገር #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #እምነት #ቃል #መዳን #ማድረግ #መስዋእት #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment