Popular Posts

Friday, December 8, 2017

የቅዱሳን መጻሕፍት አስፈላጊነት

ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን አውቀሃል። የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል። 2 ጢሞቴዎስ 315-17
የቅዱሳን መጻሕፍት ቃል የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው መፃሕፍት ናቸው፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት የተፃፉት በሰዎች ፍላጎት አይደለም፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት የሰው ሃሳብ አይደሉም፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ቅዱስ የእግዚአብሄር ቃላት ናቸው፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት የእግዚአብሄር ስራ ነው፡፡ ሰዎች በመንፈስ ተነድተው ነው ቅዱሳን መጻሕፍትን የፃፉት፡፡ የእግዚአብሄርን ሃሳብ ፅፈውታል
ስለዚህ ነው ቅዱሳት መፅሃፍት የህይወታችን ዋና ክፍል መሆን ያለባቸው፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር ላለን ግንኙነት ቅዱሳት መጽሃፍት ማእከላዊውን ቦታ ይይዛሉ፡፡
በምንም ነገር ባንመራ በቅዱሳት መጻሕፍት መመራት አስፈላጊና ወሳኝ ነው፡፡ ለሰው ከእግዚአብሄር ጋር ለመኖር የሚያስፈልገው እውቀት ሁሉ ቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ይገኛል፡፡ ሰውን ፍፁም ለማድረግ ቅዱሳን መጻሕፍት በቂ ናቸው፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ሰውን በእግዚአብሄር ቃል ሙሉ የማድረግ ሃይል አላቸው፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍትን የሚያውቅ ሰው የእግዚአብሄርን ፈቃድ ያውቃል፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍትን የሚረዳ ሰው የእግዚአብሄን ልብ ይረዳል፡፡
ሰው ከእግዚአብሄር ጋር በሚገባ እኩል መራመድ ከፈለገ ቅዱሳን መጻሕፍትን መፈለግ አማራጭ የሌለው ግዴታ ነው፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት እውቀትና መረዳት ሰውን በመረዳት ፍፁም ማድረግ ብቻ ሳይሆን ለተፈጠረለት ለበጎ ስራ ሁሉ የተዘጋጀ ያደርጉታል፡፡
ሰው ቅዱሳን መጻሕፍትን ሲረዳ የህይወት አላማውን በሚገባ ይረዳል፡፡ ሰው ቅዱሳን መጻሕፍትን ሲያውቅ ለተፈጠረለት ለመልካም ስራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆናል፡፡ እግዚአብሄር ቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ያስቀመጠውን በረከት እጅግ ድንቅ ነው፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ለአንዳንድ በጎ ስራ ብቻ አይደለም የሚያዘጋጁት ነገር ግን ሰው ቅዱሳን መጻሕፍትን ሲያውቅ አለ ለሚባለው ለበጎ ስራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆናል፡፡
ቅዱሳን መጻሕፍት ሰውን ፍፁምና ለበጎ ስራ ሁሉ የተዘጋጀ የሚያደርጉት ለሚያነባቸውና ለሚረዳቸው ሰው የሚከተሉትን እጅግ በጣም አስፈላጊ ጥቅም በመስጠት ነው፡፡
1.      ቅዱሳን መጻሕፍት ለትምህርት ይጠቅማሉ
ቅዱሳን መጻሕፍት የደህንነትን እውቀት ያካፍላሉ፡፡ ስለእግዚአብሄር የጥንቱ የመጀመሪያው አላማው ፣ ስለእግዚአብሄር ፈቃድ ፣ ስለእግዚአብሄር መንገድ ትክክለኛውን የነጠረ እውቀት የሚሰጡን ቅዱሳን መጻሕፍት ብቻ ናቸው፡፡ ማናቸውም መጻሕፍት የሚናገሩት ቃል ከቅዱሳን መጻሕፍት ሃሳብ ጋር ካልተስማማ የስህተት አስተማሪዎች ናቸው፡፡ የማንኛውም ሃሳብ ማጣቀሻ ስህተት ይሁን ትክክል ለመመዘን ስልጣን ያላቸው ቅዱሳን መጻሕፍት ናቸው፡፡  
2.     ቅዱሳን መጻሕፍት ለተግሣጽ ይጠቅማሉ
ቅዱሳን መጻሕፍት እንደ መስታወት ናቸው፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ብቻ ናቸው የቀደመውን ኦሪጅናል መልካችንን የሚያውቁትና የሚያሳዩን ከቀደመው መልካችችን ከተለወጥን የሚነግሩን፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ብቻ ናቸው ከእግዚአብሄር ኦሪጅናል ሃሳብ ዝንፍ ስንል የሚገስፁን፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ብቻ ናቸው እንደቃሉ የማይሄድን ሰው ለመገሰፅ ማንንም የማይፈሩት፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ብቻ ናቸው ተመለስ አያዋጣህም የሚሉት፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ብቻ ናቸው ያለንበትን ትክክለኛውን ቦታ ካለማመቻመች የሚነግሩን፡፡   
3.     ቅዱሳን መጻሕፍት ልብንም ለማቅናት ይጠቅማሉ
ልብ የህይወታችን አማካኝ ክፍል ነው፡፡ ልብ የህይወታችን ምንጭ ነው፡፡ ልባችን ከተበላሸ ህይወታችን ይበላሻል፡፡ ልባችን ከተስተካከለ በቅፅበት ህይወታችን ይስተካከላል፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ሌላው የማይደርስበትን ልብን የመድረስ ሃይል አላቸው፡፡ ልብ በጥንቃቄ ካልተያዘ ጥርጥር ሊሞላና ከእምነት ሊያፈነግጥ ይችላል፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ልብን ያቀናሉ፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ልብን ወደቃሉ ይመልሳሉ፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት ልብን ወደ እግዚአብሄር መንገድ ለመመለስ ሙሉ ጥበብ  አላቸው፡፡
4.     ቅዱሳን መጻሕፍት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማሉ
ቅዱሳን መጻሕፍት ልብን የሚያሳርፍ ምክር አላቸው፡፡ የቅዱሳን መጻሕፍትን ምክር ተቀብሎ የሚስት ሰው አይገኝም፡፡  መፅሃፍ ቅዱስ በእውነት ይመክራል፡፡ የእግዚአብሔርን የልብ ሃሳብ የምናገኘው በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ነው፡፡ ቅዱሳን መጻሕፍት የሚመከር ሰው በእግዚአብሄር መንፈስ ይመከራል፡፡ የቅዱሳን መጻሕፍት ምክር የማይረባውን እንዳንከተል የሚጠቅመውን እንድንይዝ ምክርን ይለግሳል፡፡ ከመፅሃፍ ቅዱስ ውጭ ትክክለኛውምን መንገድ ፅድቅን ከፈለግን እንሳሳታለን፡፡
እግዚአብሄርን በሙላት የምንከተል ለበጎ ስራ ሁሉ የተዘጋጀን ፍፁማን ሰዎች የሚያደርግን የቅዱሳት መፅሃፍት እውቀት ነው፡፡
ከሕፃንነትህም ጀምረህ ክርስቶስ ኢየሱስን በማመን፥ መዳን የሚገኝበትን ጥበብ ሊሰጡህ የሚችሉትን ቅዱሳን መጻሕፍትን አውቀሃል። የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል። 2 ጢሞቴዎስ 315-17
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እግዚአብሄር #ምክር #ቃልኪዳን #ተግሳፅ #ትምህርት #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ቅዱሳትመፅሃፍት  #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #የእግዚአብሄርመንፈስ #የእግዚአብሄርቃል

No comments:

Post a Comment