Popular Posts

Tuesday, December 26, 2017

አንድነትን ለመጠበቅ የሚጠቅሙ ምክሮች

በአንድነት ውስጥ ብቻ የተቀመጠ ታላቅ እምቅ ጉልበት አለ፡፡ አንድነትን መፈለግ ጤነኝነት ነው፡፡ አንድነት ግን በምኞት ብቻ አይመጣም፡፡ አንድ ለመሆን በመፈለጋችን ብቻ አንድነት አይመጣም፡፡
አንድነት በእድል አይመጣም፡፡ አንድነት ከሌለን ስላልሰራንበት ነው እንጂ እድለኛ ስላልሆንን አይደለም፡፡ አንድ ከሆንን አንድ የሆነው የአንድነትን መንገድ ተረድተን በትጋት ስለሰራንበት እንጂ እድለኛ ስለሆንን አይደለም፡፡
አንድነት ቅፅበታዊ አይደለም፡፡ አንድነት ረጅም ቀጣይነት ያለው ትጋትን የሚጠይቅ ግብ እንጂ በቅፅበት የሚመጣ ነገር አይደለም፡፡
በአንድነት ውስጥ የታመቀ እጅግ ታላቅ ጉልበት አለ፡፡ ያንን ታላቅ ጉልበት መጠቀም የምንችለው በአንድነት ስንቆም ብቻ ነው፡፡ በአንድነት ውስጥ ያለውን ጥቅም ለመጠቀም ለአንድነት ትጋትን መማሳየት ይኖርብናል፡፡
አንድ ሰው እንዴት ሺህን ያሳድድ ነበር? ሁለቱሳ እንዴት አሥሩን ሺህ ያሸሹ ነበር? ዘዳግም 32፡30
አንድነት ለሰነፎች እና ለልፍስፍሶች አይደለም፡፡ ማንም መንገደኛ አንድነትን ሊረብሽ ይችላል፡፡ አንድነትን ለመጠበቅ ግን ትጋትና ጥንካሬ ይጠይቃል፡፡ ማንም ሰው በስንፍና አንድነትን ሊያፈርስ ይችላል በአንድነት ውስጥ የተቀመጠውን ጠቅም ለመጠቀም ግን ጥበብና ማስተዋል ይጠይቃል፡፡ ማንም ሰው በስንፍና አንድነትን ሊያፈርስ ይችላል ነገር ግን አንድነት በትጋት ይጠበቃል፡፡
አንድነት በልባችን እኛን ለማይመስል ሰው ስፍራን ማዘጋጀት ይጠይቃል፡፡ ማንም መንገደኛ የሚመስለውንና የሚመቸውን ይሰበስባል፡፡ ማንም መንገደኛ አዎ አዎ የሚለውን ሁሌ ሃሳቡን የሚቀበለውን ይወዳል፡፡ ማንም መንገደኛ ከእርሱ የተለየወን ሰው ይጥላል፡፡ ነግር ግን ለአንድነትና ስለላቀ ውጤት የማይመስሉንን ሰዎች የሚቀበል የልብ ስፋት ይጠይቃል፡፡
ማንም ሰው የእርሱ ሃሳብ ትክክለኛ ይመስለዋል፡፡ አንድነት ከእኛ የተለየ የሚያስቡትን ሰዎች ሃሳብ ማስተናገድ ይጠይቃል፡፡ ሞኝ ትክክለኛ ስለመሰለው ስለራሱ ሃሳብ የሌሎችን ሰዎች ሁሎ ሃሳብ ሊጥል እና አንድነትን ሊረብሽ ይችላል፡፡
አንድነት ተመሳሳይነት አይደለም፡፡ አንድነት የተለያዩ ሰዎች ለአንድ አላማ መስራት ነው፡፡ ሰውን ሁሉ ተመሳሳይ ለማድረግ የሚፈትነውን ማለፍ ካላለፍን ለእንድነት መስራት አንችልም፡፡ የተለያዩ ሰዎችን ማስተናገድ ፈተና ነው፡፡ ሁሉም ሰው ተመሳሳይ ቢሆን ይቀላል፡፡ ሰው ለሁሉም ሰው አንድ ህግ አውጥቶ ሁሉም አንድ እያሰቡ ፣ ሁሉም እንድ እየተናገሩና ሁሉም አንድ እንዲኖሩ ይመኛል፡፡ ሰው ሁሉንም ተመሳሳይ ለማድረግ ተስደፋ ካልቆረጠ አንድነት የማይታሰብ ነው፡፡
አንድነት የተለያዩ ሰዎች ራሳቸውን እንዲሆኑና ነገር ግን ለአንድ አላማ እንዲሰሩ ማድረግ መቻል ነው፡፡ ሰዎችን ሁሉ ተመሳሳይ ለማድረግ መሞከር ሰዎችን ሁሉ መግደልና በሰዎችን ውስጥ ያለውን የተለያየ እምቅ ጉልበትን ማባከን ነው፡፡
እንዲያውም አንድነት ማለት እያንዳንዱ የራሱን ስራ መስራት ማለት እንጂ አንድ ጣራ ስር መሰብሰብ ፣ አንድ አይነት መልክ መያዝ አንድ አይነት አስተሳሰብ ማሰብና አንድ አይነት ነገር መናገር አይደለም፡አንድነት ማለት በአንድ አለማ ስር በመሆን እያንዳንዱ የተሰጠውን ስራ የራሱን ልዩ ስራ መስራት ማለት ነው፡፡
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ራእይ #መዳን #እምነት #አንድነት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ህብረት #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #አላማ #ግብ #ፅናት #ትግስት #ትጋት

No comments:

Post a Comment