Popular Posts

Friday, December 9, 2016

ጸጋዬ ይበቃሃል !

በክርስትና ህይወታችን ብዙ የሆኑልን መልካም ነገሮች አሉ፡፡ ስለሆነልን ነገሮች ሁሉ እግዚአብሄርን ሁል ጊዜ እናመሰግነዋለን፡፡ ብዙም እንዲሆኑልን የምንፈልጋቸው ነገሮች ደግሞ አሉ፡፡ ደግሞም ጸልየን ለምነን እንደጠበቅነው ያልሆኑልን ነገሮች ደግሞ እንዳሉ ማመንም ወሳኝ ነው፡፡
በህይወታችን እንዲሆኑልን ጠይቀን እንዳሰብነው ስላልሆኑ ነገሮች ምን ማድረግ እንደሚገባን የእግዚአብሄር ቃል ምን እንደሚል ማወቅ ያሳርፈናል፡፡  
ሃዋሪያው ጳውሎስ በህይወቱ ስለነበረው ድካም እንደፀለየ እንደለመነ እንመለከታለን፡፡ ምንም ቢለምን ሊሆንለት አልቻለም፡፡ ደጋግሞ ስለዚያ ነገር እግዚአብሄርን ሲለምን እናየዋለን፡፡
ስለዚህ ነገር ከእኔ እንዲለይ ሦስት ጊዜ ጌታን ለመንሁ። 2ኛ ቆሮንቶስ 12፡8
ደስ የሚለው ነገር ግን ለምነን ነገሩ ባይሆንም እንኳን በእግዚአብሄር መንግስት ውስጥ ሁል ጊዜ መንገድ አለ፡፡ እግዚአብሄር ለሁሉ መፍትሄ አለው፡፡ ከፊታችን ያላነሳውን ተራራ እንዴት እንደምናልፈው የሚያበረታበት መንገድ አለው፡፡
በእግዚአብሄር መንግስት ውስጥ ያበቃና የተቆረጠ ተስፋ የሌለው ነገር የለም፡፡ ወደ እግዚአብሄር ፀልየን የማይመለስ መልስ የለም፡፡ እግዚአብሄር ሁሉንም ይመልሳል፡፡ እግዚአብሄር ግን የሚመልሰው እኛ በጠበቅነው መንገድ ላይሆን ይችላል፡፡ እግዚአብሄር ግን ሁሌ ይመልሳል፡፡
እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ። 2ኛ ቆሮንቶስ 12፡9
በእግዚአብሄር ዘንድ የማይቻል ፣ የማይታለፍና የማይሆን ነገር የለም፡፡ ከፊታችን ያለውን ውሃ ካላደረቀው በውሃ ውስጥ ባለፍን ጊዜ በውሃው የማንሰጥምበትን ፀጋ ሰጥቶናል ማለት ነው፡፡ የእሳቱን ነበልባል ካላጠፋው በእሳት ውስጥ ሳንቃጠል የምናልፍበት ፀጋ በውስጣችን አለ ማለት ነው፡፡ ተራራውን ዘወር ካላደረገው ተራራውን የምንወጣበትና የምናልፍበት የሚያስችል ሃይል ተሰጥቶናል ማለት ነው፡፡
እንደ እኛ አጠባበቅ እግዚአብሄር ላልመለሳቸው ፀሎቶች የእግዚአብሄ አምላካዊ መልስ "ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማል" የሚል ነው፡፡
ደስ የሚለው ነገር በሁለቱም አሸናፊው እኛ ነን፡፡ እግዚአብሄር ለእኛ ነው፡፡ እግዚአብሄር ከእኛ ጋር ነው፡፡ እግዚአብሄር ባእኛ  ወስጥ ነው፡፡
ጸጋዬ ይበቃሃል!
ጸጋዬ ይበቃሃል!
ጸጋዬ ይበቃሃል!
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #መሪ #ፀጋ #የሚያስችልሃይል #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ትጋት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ፅድቅ #እግዚአብሄርንመምሰል #ራስንመግዛት #ልብ

No comments:

Post a Comment