Popular Posts

Saturday, December 24, 2016

ወንድ ልጅ

ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል። ኢሳይያስ 9፡6
ኢየሱስ የእግዚአብሄር ድንቅ ስጦታ ነው፡፡ ኢየሱስ ወደ ምድር ሲወለድ ከተገለፀበት ስሞች መካከል አንዱ ይህ ነበር፡፡
ኢየሱስ በምድር ላይ የነበረውን ጨለማ የመግፈፍ ታላቅ ሸክምን በጫንቃው ላይ ተሸክሞ ነበር ወደምድር የመጣው፡፡ ሰው ሁሉ የእግዚአብሄርን አላማ በማይረዳበትና በጠላት የማታለል እስራት ውስጥ በነበረበት ጊዜ ኢየሱስ ብቻ ነበር ለእውነት ሊመሰክልር ወደ ምርድ የመጣው፡፡
ጲላጦስም፦ እንግዲያ ንጉሥ ነህን? አለው። ኢየሱስም መልሶ፦ እኔ ንጉሥ እንደ ሆንሁ አንተ ትላለህ። እኔ ለእውነት ልመሰክር ስለዚህ ተወልጃለሁ ስለዚህም ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ከእውነት የሆነ ሁሉ ድምፄን ይሰማል አለው። ዮሃንስ 18፡37
በብቸኝነት በምድር ላይ የተገኘውና ሰዎችን ወደ እውነት ለመምራት ሸክምና ሃላፊነትን የወሰደው፡፡ ስለዚህ ነው ኢየሱስ የአለምን ህዝብ ወደ እውነትና ወደ ብርሃን የመምራት ሃላፊነት በጫንቃው ላይ የነበረው፡፡
ደግሞም ኢየሱስ፦ እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ፤ የሚከተለኝ የሕይወት ብርሃን ይሆንለታል እንጂ በጨለማ አይመላለስም ብሎ ተናገራቸው። ዮሃንስ 8፡12
ኢየሱስ ከተገለፀባቸው ስሞች ማዕረጎችና መካከል ድንቅ መካር የሚለውም ይገኝበታል፡፡ ኢየሱስ እውነትም መካሪ ነው ያውም ድንቅ መካሪ፡፡ በህይወት በተጨንቅንበት ጊዜ መውጫው በጨነቀን ጊዜ ምን ማድረግ እንደሚገባን ግራ በገባን ጊዜ ምን ማድርግ እንዳለብል መውጫውን የሚያሳየን ኢየሱስ ነው፡፡ መንገዱ በጠፋብን ጊዜ ሁሉ ኢየሱስ መንገድ ነው፡፡ ግራና ቀኙን የማያውቀው ሰው ኢየሱስ ሲገናኘው ምን ማድረግ እንዳለበት ማወቅ ይጀምራል፡፡  
ኢየሱስ ከዘላለም በፊት የነበረ የእግዚአብሄር ቃል ነው፡፡ ምንም በምድር የእኛን የሃጢያት እዳ ለመክፈል ሰው ሆኖ ቢመጣም ኢየሱስ ግን ከዘላለም የነበረ ኃያል አምላክ ነው፡፡ በሰው ምክኒያት ሃጢያት ወደ ምድር እንደገባ ሁሉ በሰው ምክኒያት የሃጢያት ሃይል መሻር ሰለነበረበት ኢየሱስ እንደ ሰው በስጋና በደም ተካፈለ እንጂ ኢየሱስ ምድርን የፈጠረ ለአላማው የጨከነ ሃያል አምላክ ነው፡፡ ለማዳን ብርቱ በምንም የማይበገር አለምን ያሸነፈ ሃያል አምላክ ነው፡፡
እውነተኛ አባትነትን ያሳየን ኢየሱስ ነው፡፡ ኢየሱስ እውነተኛ አሳቢ ፣ የሚጠነቀቅልን ፣ መሪያችን ፣ ታጋሽ አባት ነው፡፡ የአባት ትርጉሙ ከጠፋብን ከኢየሱስ ጋር በተገናኘን ጊዜ የአባትን ትርጉም በቅጡ እንረዳለን፡፡ የአባትነት ድርሻና ሃላፊነት ክርክር ቢነሳ ሊፈታው የሚችል አባትነቱን ያስመሰከረ ኢየሱስ ነው፡፡
ኢየሱስ የሰላም አለቃ ነው፡፡ እውነተኛ ሰላምን የፈለገ ሰው ወደ ሌላ መመልከት የለበትም፡፡ የሰላምን ትርጉም ያጣ ሰው እውነተኛ የሰላምን ትርጉም የሚረዳው በኢየሱስ ነው፡፡ ኢየሱስ የሚሰጠው ሰላም አለም እንደሚሰጠው ሰላም አይነት አይደለም፡፡ ኢየሱስ የሚሰጠው ሰላም አእምሮን የሚያልፍ ሰላም ነው፡፡ ኢየሱስ የሚሰጠው ሰላም ከአለም ጩኸትና ትርምስ በላይ የሚሰማ ልብን የሚያሳርፍ ሰላም ነው፡፡
አእምሮንም ሁሉ የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሰላም ልባችሁንና አሳባችሁን በክርስቶስ ኢየሱስ ይጠብቃል። ፊልጵስዩስ 4፡7
ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም። ልባችሁ አይታወክ አይፍራም። ዮሃንስ 14፡27
ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል። ኢሳይያስ 9፡6
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ሰላም #ድንቅመካር #ሃያልአምላክ #የሰላምአለቃ #ዘላለምአባት #ኢየሱስ #ክርስቶስ #ጌታ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #እምነት #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #አለቅነት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment