Popular Posts

Monday, December 5, 2016

የአእምሮ ብስለት ይጠይቃል

አንዳንድ ጊዜ ከምናስበው በላይ በአእምሮ ያለመብሰል በህይወታችን ሲንፀባረቅ ይታያል፡፡ ችግሩ ደግሞ አብዛኛው ሰው በሳል የሆነ ይመስለዋል፡፡ በሳል የሆነ የመሰለው ሰው ከእግዚአበሄር ቃል የብስለቱን መጠን መለካትና በእግዚአብሄር ቃል ወደከፍ ያለ የብስለት ደረጃ ለማደግ መትጋት ይገባዋል፡፡
ወንድሞች ሆይ፥ በአእምሮ ሕፃናት አትሁኑ፤ ለክፋት ነገር ሕፃናት ሁኑ እንጂ በአእምሮ የበሰሉ ሁኑ። 1ኛ ቆሮንቶስ 14:20 ብስለታችንን የምንለካባቸው መንገዶችና በሳል ሰው ያለው አመለካከት ተዘርዝረዋል፡፡

  • · በሳል ሰው ለልዩነት አክብሮት ያለው ነው
ያልበሰለ ሰው ከእርሱ የተለየ ማንኛውም ነገር ስህተት ይመስለዋል፡፡ ሰውን ሁሉ ተመሳሳይና አንድ አይነት ለማድረግ ይሞክራል፡፡ ሰው ግን ክቡር ነው እያንዳንዱ ሰው እንደ የሁኔታው ሊያዝ ይገባዋል፡፡ ስለዚህ ያልበሰለ ሰው ከእርሱ ለተለየው ሰው ምንም ቦታ የለውም፡፡

  • · በሳል ሰው ለትንንሽ ሰዎች ባለው አክብሮት ይታወቃል

በሳል ሰው ራሱን በሚገባ ስሚያውቅ ሌሎችን ለመድረስ ሰዎችን አይመርጥም፡፡ በሳል ሰው ሰውን በሰውነቱ እንጂ በሌላ በምንም ነገር አይመዝንም፡፡ በሳል ሰው ሰውን የሚያውቀው በክርስቶስ እንጂ በሌላ አይደለም፡፡
እርስ በርሳችሁ በአንድ አሳብ ተስማሙ፤ የትዕቢትን ነገር አታስቡ፥ ነገር ግን የትሕትናን ነገር ለመሥራት ትጉ። ልባሞች የሆናችሁ አይምሰላችሁ። ሮሜ ሰዎች 12፡16

  • · በሳል ሰው የራሱን ሃሳብ ብቻ አይፈልግም

በሳል ሰው የሌሎችም ሃሳብ ቢደረግ እንደሚሳካ ያምናል፡፡ በሳል ሰው በሌሎችም እግዚአብሄር እንደሚጠቀም ያምናል፡፡ በሳል ሰው ለአንድነት ራሱን ትሁት ያደርጋል፡፡
በክርስቶስም አንዳች ምክር ቢሆን፥ የፍቅር መጽናናት ቢሆን፥ የመንፈስ ኅብረት ቢሆን፥ ምሕረትና ርኅራኄ ቢሆኑ፥ ደስታዬን ፈጽሙልኝ፤ በአንድ አሳብ ተስማሙ፥ አንድ ፍቅር አንድም ልብ አንድም አሳብ ይሁንላችሁ፤ ፊልጵስዩስ 2፡1-2

  • · በሳል ሰው በደረሰበት ቦታ ሁሉ ላለው ስልጣን እውቅና ይሰጣል፡፡

በሳል ሰው የስልጣንን ጥቅምና አላማ ስለሚረዳ ለስልጣን አክብሮት አለው፡፡ በሳል ሰው ስልጣንንየሚያከብረው ለታይታ ሳይሆን ሁልጊዜ ነው፡፡
እኔ ደግሞ ለሌሎች ተገዥ ነኝና፥ ከእኔም በታች ጭፍራ አለኝ፤ አንዱንም፦ ሂድ ብለው ይሄዳል፥ ሌላውንም፦ ና ብለው ይመጣል፥ ባሪያዬንም፦ ይህን አድርግ ብለው ያደርጋል አለው። ማቴዎስ 8፡9

  • · በሳል ሰው ለቁሳቁስ ዝቅተኛ አመለካከት ያለው ሰው ነው፡፡

ቁሳቁስን የሚያከብር ሰው በሳል ሰው አይደለም፡፡ በሳል ሰው ቁሳቁስ ካላቸውን ደረጃ በላይ አጋኖ አያያቸውም፡፡ በሳል ሰው ከቁስና ከውጭ እይታ በላይ ለልብ እውቅና ይሰጣል፡፡
ወደ ዓለም ምንም እንኳ አላመጣንምና፥ አንዳችንም ልንወስድ አይቻለንም፤ ምግብና ልብስ ከኖረን ግን፥ እርሱ ይበቃናል። 1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 6፡7-8
እርስዎም ስድስተኛውን ይጨምሩበት ?
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ልብ #ቁሳቁስ #አላማ #መሰረታዊፍላጎት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ጥሪ #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #አንድነት #ትህትና #አክብሮት #ስልጣን #መሪ

No comments:

Post a Comment