Popular Posts

Friday, January 13, 2017

በእግዚአብሔር እመኑ

ልባችሁ አይታወክ፤ በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ። ዮሐንስ 141
ኢየሱስ አለ "በእግዚአብሄር እመኑ"፡፡ በእግዚአብሄር የማያምን ሰው አለ ወይ የሚል ጥያቄ ይጠየቅ ይሆናል፡፡ ምክኒያቱም ሁሉም ሰው በእግዘኢአብሄር እንደሚያመን ይናገራል፡፡ እግዚአብሄርን የሚያምን ሰው አለ፡፡ እግዚአብሄርን የማያምን ሰው አለ፡፡ ሁሉም ሰው እግዚአብሄርን አያምንም፡፡
እምነት የሚለካው በስራ ነው፡፡ ሰው አግዚአብሄርን አምናለሁ እያለ እግዚአብሄርን የሚያምን ሰው ስራን ካልሰራ ወይም እግዚአብሄርን እንደሚያምን ሰው ካልኖረ እግዚአብሄርን እንደማያምን ግልፅ ነው፡፡ 
እምነት በአይን የሚታይ ነገር አይደለም እምነት ግን በድርጊት ይገለፃል፡፡ በእግዚአብሄር የሚያምን ሰው የሚያደርገው ነገር አለ፡፡ በእግዚአብሄር የማያምን ሰው የሚያደርገው ነገር ደግሞ አለ፡፡ በእግዚአብሄር የሚያምን ሰው የማያደርገው ነገር አለ፡፡ በእግዚአብሄር የማያምን ሰው የማያደርገው ነገር አለ፡፡
እግዚአብሄርን ማመናችንና አለማመናችን የሚያሳዩ ምልክቶች
በእግዚአብሄር የሚያምን ያርፋል
ሰው በእግዚአብሄር አምናለሁ እያለ ካላረፈ በእግዚአብሄር አላመነም፡፡ ያመነ ሰው ልቡ አይታወክም፡፡ ያመነ ሰው ሰላሙን አያጣም፡፡
ስለዚህ ምድር ብትነዋወጥ፥ ተራሮችም ወደ ባሕር ልብ ቢወሰዱ አንፈራም። መዝሙር 46፡2
ሰው የራሱን ደረጃ በራሱ ከፍ አድርጎ ከሰቀለ በእግዚአብሄር አያምንም፡፡ የሰውን ክብር የሚፈልግ ሰው እግዚአብሄርን አላመነም፡፡ 
እናንተ እርስ በርሳችሁ ክብር የምትቀባበሉ ከአንዱም ከእግዚአብሔር ያለውን ክብር የማትፈልጉ፥ እንዴት ልታምኑ ትችላላችሁ? ዮሐንስ 5፡44
ያመነ ሰው ራሱን ለማዋረድ አይከብደውም
ኢየሱስ አብ ሁሉን በልጁ እንደ ሰጠው ከእግዚአብሔርም እንደ ወጣ ወደ እግዚአብሔርም እንዲሄድ አውቆ፥ ከእራት ተነሣ ልብሱንም አኖረ፥ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ፤ በኋላም በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ። ዮሐንስ 13፡3-5
ሰው በሁኔታዎች ሰላሙን ካጣ በእግዚአብሄር አላመነም፡፡
ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም። ልባችሁ አይታወክ አይፍራም። ዮሐንስ 14፡27
በአንዳንደ ነገሮች እግዚአብሄር እንደማያስፈልገው የሚያስብ ሰው በእግዚአብሄር አልታመነም፡፡
እግዚአብሔርን ፈልጉት ትጸናላችሁም፤ ሁልጊዜ ፊቱን ፈልጉ። መዝሙር 105፡4
ሰው ከሰው እድገትን ከጠበቀ በእግዚአብሄር አላመነም፡፡ ሰው ሰውን እንዲያነሳው ተስፋ ካደረገ እግዚአብሄርን አልታመነም፡፡ ሰው በአንድ ጊዜ በሰውም ላይ በእግዚአብሄር ላይ ሊታመን አይችልም፡፡
ክብር ከምሥራቅ ወይም ከምዕራብ ወይም ከምድረ በዳ የለምና፤ መዝሙር 75፡6
ሰው ስለስኬቱ በሰው ላይ ልቡን የሚጥል ሰው በእግዚአብሄርን አላመነም፡፡
እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ በሰው የሚታመን ሥጋ ለባሹንም ክንዱ የሚያደርግ ልቡም ከእግዚአብሔር የሚመለስ ሰው ርጉም ነው። ኤርምያስ 17፡5
ሰው ለእግዚአብሄር ላለመስራት ከሰሰተ በእግዚአብሄር አላመነም፡፡ ሰው ሲያምን ለእግዚአብሄር ሁሉን ነገሩን ይሰጣል፡፡ ሰው ለእግዚአብሄር ከመስጠት የሚሰስተው ነገር ካለ አልታመነም ማለት ነው፡፡
አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፦ ጌታ ሆይ፥ ካልዘራህባት የምታጭድ ካልበተንህባትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ፥ መክሊትህ አለህ አለ። ማቴዎስ 25፡24-25
ያመነ ሰው ጌታን በትግስት ይጠብቃል
ሰው እግዚአብሄርን ለመጠበቅ ትግስት ካጣ በእግዚአብሄር አላመነም፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን አመጣጥ ካልታገሰ እምነት ጎድሎታል፡፡
የታመነ ሰው እጅግ ይባረካል፤ ባለጠጋ ለመሆን የሚቸኵል ግን ሳይቀጣ አይቀርም። ምሳሌ 28፡20
እጦትን የሚፈራ ሰው በእግዚአብሄር አልታመነም 
የታመነ ሰው እጦትን አይፈራም፡፡ የታመነ ሰው እጦት እንዳይደርስበት የማይገባውን አያደርግም፡፡ የታመነ ሰው እጦትን ይንቃል፡፡ የታመነ ሰው እጦት ምንም እንደማያመጣና ሁሉን የሚችለው ኃይልን በሚሰጠው በክርስቶስ እንደሆነ ያምናል፡፡
መዋረድንም አውቃለሁ መብዛትንም አውቃለሁ፤ በእያንዳንዱ ነገር በነገርም ሁሉ መጥገብንና መራብንም መብዛትንና መጉደልን ተምሬአለሁ። ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ። ፊልጵስዩስ 4፡12-13
ስለህይወቱ የሚጨነቅ ሰው እግዚአብሄርን አልታመነም
እግዚአብሔር ግን ዛሬ ያለውን ነገም ወደ እቶን የሚጣለውን የሜዳን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከሆነ፥ እናንተ እምነት የጎደላችሁ፥ እናንተንማ ይልቁን እንዴት? እንግዲህ፦ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን? ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤ ማቴዎስ 6፡30-31
ባለጠግነት ጥበብና ሃይል ሀይወቴን ያቃኑታል ብሎ የሚያስብ ሰው በእግዚአብሄር አልታመነም፡፡
እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ጠቢብ በጥበቡ አይመካ፥ ኃያልም በኃይሉ አይመካ፥ ባለ ጠጋም በብልጥግናው አይመካ፤ ነገር ግን የሚመካው፦ ምሕረትንና ፍርድን ጽድቅንም በምድር ላይ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን በማወቁና በማስተዋሉ በዚህ ይመካ፤ ደስ የሚያሰኙኝ እነዚህ ናቸውና፥ ይላል እግዚአብሔር፡፡ ኤርምያስ 9፡23-24
ልባችሁ አይታወክ፤ በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ። ዮሐንስ 14፡1
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #ሃሳብ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #እምነት #ቃል #አእምሮ #ማደስ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment