Popular Posts

Monday, January 16, 2017

በመዋረዳችን እንጠቀማለን

ጌታን ኢየሱስን የምንከተል ሁላችን በእግዚአብሄር ፊት የከበርን ነን፡፡
ልጁ በብዙ ወንድሞች መካከል በኵር ይሆን ዘንድ፥ አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና፤ አስቀድሞም የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፤ የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፤ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው። ሮሜ 8፡29-30
ስለዚህ ነው በምድር ላይ የምናልፍባቸው ከፍታዎችና ዝቅታዎች ሊያሸንፉን የማይችሉት፡፡ ጠላት እኛን ለመጣል የሚያመጣውን እንኳን እግዚአብሄ ለከፍታችን ይጠቀምበታል፡፡
በአንድም በሌላም መልኩ የሚዋርዱ ነገሮች በህይወታችን ይመጣሉ፡፡ ነገሮች ሊያዋርዱን በጉድለት በመጡ መጠን እግዚአብሄር የሚክስበት የራሱ መንገድ አለው፡፡ በጎደለን ቅፅበት የሚሞላ የእግዚአብሄር ፀጋ በህይወታቸን ይሰራል፡፡
በሳይንስ ስንማር አንድ ምንም ውሃ ያልያዘ ብርጭቆ ባዶ አይደለም ተብለን ተምረናል፡፡ ባዶው ብርጭቆ ውሃ ባይኖረውም ውሃው የጎደለበትን ቦታ ሁሉ የሚሞላ በባዶ አይናችን የማናየው አየር አለ፡፡
የእግዚአብሄርም አሰራር እንዲዚሁ ነው፡፡ ሰይጣን ሊያጠቃን የሚችለው በሚታየው ነገር ብቻ ነው፡፡ በሚታየው ነገር ሊያዋርደን ሲመጣ እግዚአብሄር በማይታየው በከበረው በተሻለው ነገር ጉድለታችንን ይሞላል፡፡ በሚታየው ነገር ተዋረድን ማለት በማይታየው ነገር ከበርን ማለት ነው፡፡  
በሚታይ ነገር 100 እጅ ሞልቶልኛል የሚያዋርደኝ ምንም ነገር የለም የሚል ማንም ሰው እንደሌለ ሁሉ ሁላችንም ዘወትር የሚያበረታውን የእግዚአብሄርን ፀጋ እንፈልጋለን፡፡ በጎደለን በማንኛውም እጅ የእግዚአብሄ ፀጋ ስለሚሞላብን ሁልጊዜ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን፡፡ ለእኛ መዋረዳችን እንኳን በሌላ መልኩ ጥቅም ነው፡፡
እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ። 2ኛ ቆሮንቶስ 12፡9
አዳምና ሄዋን በሃጢያት ከመውደቃቸው በፊት ምንም ልብስ ባይለብሱም ራቁትነታቸው አይታይም ነበር፡፡ ራቁትነታቸውን የሚሸፍን የእግዚአብሄርምን ፀጋ ለብሰው ነበር፡፡  
የሚታይ ነገር ሲጎድል የእግዚአብሄር ፀጋ የሚያስችለን ሃይሉ ቦታውን እየያዘ ይመጣል፡፡ የሚታይ ነገር ሲጎድል የማይታየው የእግዚአብሄር ሃይል እያበረታን ይመጣል፡፡ በነገሮች ስንዋረድ በእግዚአብሄር አሰራር ከፍ ከፍ እንላለን፡፡ በመዋረዳችን በሚያበረታ ፀጋ ለእኛ ማሸነፍ ሁልጊዜ ነው፡፡
ነገር ግን በክርስቶስ ሁልጊዜ ድል በመንሣቱ ለሚያዞረን በእኛም በየስፍራው ሁሉ የእውቀቱን ሽታ ለሚገልጥ ለአምላክ ምስጋና ይሁን፤ 2ኛ ቆሮንቶስ 2፡14
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ክብር #መዋረድ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #አንድነት #ፀጋ  #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment