Popular Posts

Sunday, January 1, 2017

እረፍት ከስራ ይቀድማል

ሰውን የፈጠረው እግዚአብሄር ነው፡፡ እግዚአብሄር ሰውን ሲፈጥረው ለአላማው ነው፡፡ እግዚአብሄር ለሰው የሚያስፈልገውን ማንኛውንም ነገር በአምስት ቀናት ውስጥ ፈጠረ ሰራና አዘጋጀ፡፡
እግዚአብሄር ሰውን የፈጠረው ሊያርፍ ሲል በስድስተኛው ቀን ነው፡፡ የመጀመሪያው የሰው ስራ የነበረው እረፍት ነው፡፡ አሁንም ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ የሰው የመጀመሪያውና በጣም አስፈላጊው ሃላፊነት ማረፍ ነው፡፡ ያላረፈ ሰው ምንም ሊሰራ አይችልም፡፡ የሰውም ፍሬያማነት የሚለካው በእረፍቱ መጠን ብቻ ነው፡፡
ሰው በህይወት ስኬታማ እንዲሆን ካስፈለገ ማረፍ አለበት፡፡ ሰው በእግዚአብሄር ካረፈ ብቻ ነው ትርጉንም ያለው ስራ የሚሰራው፡፡ ሰው በእግዚአብሄር ከተደገፈ ብቻ ነው ፍሬያማ የሚሆነው፡፡
ስለዚህ ነው ገና ሃጢያተች ሆነንን ሳለን በሃጢያት ምክኒያት እረኛ እንደሌላቸው በጎች ተቅበዝብዘን ሳለን ኢየሱስ የሃጢያታችን እዳ ለመክፈል ወደምድር መጣ፡፡ ኢየሱስ የሃጢያታችንን እዳ ሙሉ ለሙሉ እንደከፈለ ተፈፀመ አለ፡፡
ማንም ሰው የእግዚአብሄር አላማ ውስጥ ለመግባት ኢየሱስ በመስቀል ላይ በሰራው የማዳን ስራ ላይ መደገፍ አለበት፡፡ ሰው እግዚአብሄርን ለማስደሰት በእግዚአብሄር በሚያስችል ሃይሉ በፀጋው ላይ ማረፍ አለበት፡፡
ሥራው ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ምንም እንኳ ቢፈጸም፦ እንዲህ፦ ወደ ዕረፍቴ አይገቡም ብዬ በቁጣዬ ማልሁ እንዳለ፥ እኛስ ያመንን ወደ ዕረፍቱ እንገባለን። ዕብራውያን 4፡3
ከምንም ስራ ቀዳሚው ማረፍ ነው፡፡ ለምንም ስራ የጉልበት ምንጩ እረፍት ነው፡፡ የምንም የእግዚአብሄር ስራ መመዘኛው እረፍት ነው፡፡ በእግዚአብሄር ዘንድ የሚጀመረው ከማረፍ ነው፡፡  በራሳችን ምንም ማድረግ ስለማንችል ስራ ተሰርቶ ሳይሆን የሚታረፈው ታርፎ ነው የሚሰራው፡፡ ፍሬ ለማፍራ በቅርንጫፉ መታመን ይጠይቃል፡፡
እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፥ እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል። ዮሃንስ 15፡5
ከመስራታችን በፊት እግዚአብሄር አስቀድሞ እየሰራ እንደሆነ ማወቅና ማረፍ አለብን፡፡ እኛ ብቻችንን እንደምንሰራ ካሰብን ስራው ውጤታማ እየሆንም፡፡
ኢየሱስ ግን፦ አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል እኔም ደግሞ እሠራለሁ ብሎ መለሰላቸው። ዮሃንስ 5፡17
ከመፀለያችን በፊት የሚያስፈልገንን ሳንለምን በፊት እንደሚያውቅ በማመን ማረፍ ውጤታማ ያደርገናል፡፡
ስለዚህ አትምሰሉአቸው፤ ሳትለምኑት አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃልና። ማቴዎስ 6፡8
የእግዚአብሄርን ስራ ከመስራታችን በፊት ወጪው ሁሉ በእርሱ እንደሆነ በመረዳት ማረፍ ይጠበቅብናል፡፡
የመለኮቱ ኃይል፥ በገዛ ክብሩና በበጎነቱ የጠራንን በማወቅ፥ ለሕይወትና እግዚአብሔርን ለመምሰል የሚሆነውን ነገር ሁሉ ስለ ሰጠን፥ በእግዚአብሔርና በጌታችን በኢየሱስ እውቀት ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ። 2 ጴጥሮስ 1፡2-3
ለጌታ ስለሰጠን እንደማይጎድልብን እርሱ እረኛችን እንደሆነ በማረፍ ነው፡፡
ስጡ ይሰጣችሁማል፤ በምትሰፍሩበት መስፈሪያ ተመልሶ ይሰፈርላችኋልና፥ የተጨቈነና የተነቀነቀ የተትረፈረፈም መልካም መስፈሪያ በእቅፋችሁ ይሰጣችኋል። ሉቃስ 6፡38
ሌላውን ይቅር የምንለውና የምንምረው እግዚአብሄር በእጅጉ እንደማረን ስላወቅንና በምህረቱ እርፍ ስላልን ነው፡፡

ከዚያ ወዲያ ጌታው ጠርቶ፦ አንተ ክፉ ባሪያ፥ ስለ ለመንኸኝ ያን ዕዳ ሁሉ ተውሁልህ፤ እኔ እንደ ማርሁህ ባልንጀራህ የሆነውን ያን ባሪያ ልትምረው ለአንተስ አይገባህምን? አለው። ማቴዎስ 18፡32-33
መልካም የምናደርገው ለመዳን ሳይሆን ስለዳንን መሆኑን በማወቅ ማረፍ ፍሬያማ ያደርገናል፡፡
ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም። እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን። ኤፌሶን 28-10
ሌላውን የምንወደው በራሳችን ጉልበት እንዳይደለ ነገር ግን የእግዚአብሄ ፍቅር በልባችን እንደፈሰሰ በማመንና በማረፍ ካልሆነ አይሳካልንም፡፡    
በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ፈሰሰ ተስፋ አያሳፍርም። ሮሜ 5፡5
እውነተኛ ስራ እውነተኛ ውጤት እውነተኛ ፍሬ የሚፈራው በማረፍ ነው፡፡ ባረፍን መጠን ብቻ ነው የምንሰራው፡፡ ባረፍን መጠን ብቻ ነው የምናፈራው፡፡ በእምነት ባረፍን መጠን ብቻ ነው ውጤታማ የምንሆነው፡፡
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#እረፍት #ቅድሚያ #እምነት #መደገፍ #ሰንበት #አስቀድማችሁ #ፅድቁን #ኢየሱስ #ክርስቶስ #ጌታ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #እምነት #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ምህረት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ



No comments:

Post a Comment