Popular Posts

Tuesday, October 8, 2019

የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል



የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል፥ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት፤ ሰው ባልተወለደ ይሻለው ነበር አለ። የማቴዎስ ወንጌል 2624
በምድር ከላይ እንደእኛ የተመላለሰው ኢየሱስ ህይወቱ ይሄድ የነበረው እንደተፃፈለት ነው፡፡ ኢየሱስ የመጣው የተፃፈለትን ለመፈፀም ነው፡፡  
በዚያን ጊዜ፦ እነሆ፥ በመጽሐፍ ጥቅልል ስለ እኔ እንደ ተጻፈ፥ አምላኬ ሆይ፥ ፈቃድህን ላደርግ መጥቼአለሁ አልሁ ይላል። ወደ ዕብራውያን 10፡7
እንዲሁም በድንገት የተፈጠረ ማንም ሰው የለም፡፡ ሁላችንም በአላማ ተፈጥረናል፡፡ ይህን የእግዚአብሄርን አላማ ለመከተል ራሳችንን ስንሰጥ በህይወታችን የሚሆኑ ነገሮች ሁሉ በዚያ በእግዚአብሄር አላማ ይተረጎማሉ፡፡
ለእናንተ የማስባትን አሳብ እኔ አውቃለሁ፤ ፍጻሜና ተስፋ እሰጣችሁ ዘንድ የሰላም አሳብ ነው እንጂ የክፉ ነገር አይደለም። ትንቢተ ኤርምያስ 29፡11
እግዚአብሄርን ለሚወዱ ሰዎች ክፉ ነገሮች ለመልካምነታቸው ይሰራሉ፡፡ እንደሃሳቡ የተጠሩ ሰዎች ከግባቸው የሚያቆማቸው አንድም ክፉ ነገር የለም፡፡ እግዚአብሄር የሚወዱ ሰዎች ክፉ ነገር እንኳን ለመልካምነታቸው ይሰራል፡፡ እግዚአብሔርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ከፍቶ የሚቀር ነገር አይኖርም፡፡
መፅሃፍ ቅዱስ እግዚአብሄርን ለሚወዱ እንደ ሃሳቡ ለተጠሩ ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን የሚለው ስለዚህ ነው፡፡
እግዚአብሄርን የሚያስደንቀው ነገር የለም፡፡ ለእግዚአብሄር ድንገተኛ የሆነ ነገር የለም፡፡ ለሰው ድንገት የሆነው ነገር ሁሉ እግዚአብሄር ከመሆኑ በፊት ያውቃዋል፡፡ ሰይጣን ለክፋት ያደረግውን ነገር ሁሉ እግዚአብሄር ለበጎነት ይለውጠዋል፡፡ እግዚአብሄ ከሚጎዳ ነገር ውስጥ ጥቅምን ያወጣል፡፡ እግዚአብሄር ከበላተኛ ውስጥ የሚበላ ያወጣል፡፡  
እርሱም፦ ከበላተኛው ውስጥ መብል ወጣ፥ ከብርቱም ውስጥ ጥፍጥ ወጣ አላቸው። ሦስት ቀንም እንቈቅልሹን መተርጎም አልቻሉም። መጽሐፈ መሣፍንት 14፡14
እግዚአብሄር በማንም አይበለጥም፡፡ እግዚአብሄርን በጥበብ የሚበልጠው የለም፡፡ የሰይጣንን ነገር ራሱን ተጠቅሞ ወደበጎ ይለውጠዋል በዚያም ይባርከናል፡፡ እግዚአብሔርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ሰዎች ሰይጣን ያደረገው ነገር እንኳን ለጥፋታቸው ሳይሆን ተመልሶ ለበጎነታቸው ይሰራል፡፡ እግዚአብሔርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ሰዎች ሁሉም ነገር ተሰብስቦ ለበጎነታቸው ይሰራል፡፡
እግዚአብሔርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን። ወደ ሮሜ ሰዎች 8፡28
ከቁጥጥር ውጭ አይደለም
ብዙ ጊዜ እኛ ራሳችንን እና ነገሮችን እንደሚገባው ስለማንረዳ ነገሮች ከቁጥጥር የወጡ ይመስለናል፡፡ ነገር ግን ነገሮች ከቁጥጥር ውጭ አይደሉም፡፡ ነገሮች ገደብ አላቸው ከገደቡ ሊያልፉ አይችሉም፡፡ ሰው የሚያልፈው በተፃፈለት ነው፡፡ ሰው ከተፃፈለት በላይ ሊያልፍ አይችልም፡፡ ሰው ከሚችለው በላይ እንዲፈተን እግዚአብሄር አይፈቅድም፡፡
የተፃፈው መፈፀሚያ መሆን ከቅጣት አያስመልጥም
ክፉ ሰው የተፃፈው ነገር መፈፀሚያ የሚሆነው አውቆ አይደለም፡፡ ክፉ ሰው ክፋት የሚሰራው የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለማድረግ ብሎ አይደለም፡፡ ክፉ ሰው ክፋት የሚሰራው በራስ ወዳድነት ነው፡፡
እግዚአብሄር እውነተኛ ዳኛ ነው፡፡ እግዚአብሄር ስራውን መዝኖ የተበደለውን ሰው እንዴት እንደሚክሰው ያውቃል፡፡
አትታበዩ፥ በኩራትም አትናገሩ፤ እግዚአብሔር አዋቂ ነውና፥ እግዚአብሔርም ሥራውን የሚመዝን ነውና፥ ከአፋችሁ የኵራት ነገር አይውጣ። መጽሐፈ ሳሙኤል ቀዳማዊ 2፡3
በሌላው መበደል የእግዚአብሄርን ካሳ ስለሚያስገኝ ምንም ጉዳት የለውም፡፡ እግዚአብሄር የሌላው ሰው የሚበደለውን ስለሚክስ ሰውን ከመበደል ይልቅ በሰው መበደል መበደል ይሻላል፡፡ ሰውን መበደል የሚያስገኘው ምንም ጥቅም የለም፡፡ ሰውን መበደል ቅጣት እንጂ ጥቅም የለውም፡፡  
እንግዲህ ፈጽሞ የእርስ በርስ ሙግት እንዳለባችሁ በእናንተ ጉድለት ነው። ብትበደሉ አይሻልምን? ብትታለሉስ አይሻልምን? 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 6፡7
እግዚአብሄር ከሚበደል ሰው ጋር ስለሚወግን እና በደሉን ለመልካም ስለሚለውጥለት ሁልጊዜ የችግሩ ሳይሆን የመፍትሄው አካል ለመሆን እንጠንቀቅ፡፡
የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል፥ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት፤ ያ ሰው ባልተወለደ ይሻለው ነበር አለ። የማቴዎስ ወንጌል 26፥24
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#የእግዚአብሄርምክር #የእግዚአብሔርፈቃድ #እግዚአብሔር #እንደተፃፈ #እምነት #የሰውአሳብ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

No comments:

Post a Comment