Popular Posts

Thursday, October 24, 2019

ወደሚቀጥለው የህይወት ምዕራፍ መሸጋገሪያ ጥበብ



እያንዳንዳችን ማደግ መለወጥ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ መሸጋገር እንፈልጋለን፡፡ በህይወት ላለ ሰው ይህ ፍላጎት የጤነኛ ሰው ፍላጎት ነው፡፡
ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ገና እንዳልያዝሁት እቈጥራለሁ፤ ነገር ግን አንድ ነገር አደርጋለሁ፤ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እዘረጋለሁ፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ከፍ ከፍ ያለውን የእግዚአብሔርን መጥራት ዋጋ እንዳገኝ ምልክትን እፈጥናለሁ። ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 3፡13-14
ነገር ግን ወደሚቀጥለው ምእራፍ መሻገር ወደሚቀጥለው ምእራፍ ለመሻገር እንደመፈለግ ቀላል አይደለም፡፡ ወደሚቀጥለው ምእራፍ በጥንቃቄ ለመሻገር ጥበብ ይጠይቃል፡፡  
ሰው በፍሬያማነት ወደ ሚቀጥለው ምእራፍ የሚሻገርበትን መጽፅሃፍ ቅዱሳዊ ጥበብ እንመልከት
1.      ለእግዚአብሄር አላማ ጊዜ አለው
እግዚአብሄር ለህይወታችን ሙሉ እቅድ አለው፡፡ እኛ በፈለግንበት ጊዜ ወደ ሚቀጥለው ምእራፍ መሸጋገር አንችልም፡፡ እግዚአብሄር የህይወት እቅዳችንን በትጋት በጊዜው እየሰራው ነው፡፡ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ ለመሻገር ማድረግ የምንችለው ነገር ባለንበት ምእራፍ ላይ ታማኝ ሆነን የምእራፍ መለወጫውን ጊዜ መጠበቅ ብቻ ነው፡፡
ለሁሉ ዘመን አለው፥ ከሰማይ በታችም ለሆነ ነገር ሁሉ ጊዜ አለው። ለመወለድ ጊዜ አለው፥ ለመሞትም ጊዜ አለው፤ ለመትከል ጊዜ አለው፥ የተተከለውንም ለመንቀል ጊዜ አለው፤ መጽሐፈ መክብብ 3፡1
2.     ባለንበት ምእራፍ መቆየት
እግዚአብሄር ሁኔታዎችን ሁሉ እስኪመቻች ባለንበት ምእራፍ እንደመቆየት የመሰለ ቦታ የለም፡፡ እግዚአብሄር እንድትለውጥ እስካልመራህ ድረስ ስታደርግ የቆየኸውን እንደማድረግ ምቹ ቦታ የለም፡፡ እግዚአብሄር ሳይልህ እርምጃ መውሰድ ብዙ ዋጋ የሚያስከፍል እርምጃ ነው፡፡ ስለወደፊቱ የህይወት ምእራፍህ ግልፅ ካልሆነ ጊዜው አይደለም ማለት ነው፡፡ ስለሚቀጥለው የህይወት ምእራፍህ አቅጣጫ ምሪት ካጣህ ካለምሪት ከመንቀሳቀስ ይልቅ ስታደርግ የቆየኸውን እንደማድረግ አስተማማኝ ነገር የለም፡፡
በእስያም ቃሉን እንዳይናገሩ መንፈስ ቅዱስ ስለ ከለከላቸው በፍርግያና በገላትያ አገር አለፉ፤ በሚስያም አንጻር በደረሱ ጊዜ ወደ ቢታንያ ይሄዱ ዘድን ሞከሩ፥ የኢየሱስ መንፈስም አልፈቀደላቸውም፤ የሐዋርያት ሥራ 16፡6-7
3.     ባለንበት ምእራፍ መትጋት
ወደሚቀጥለው ምእራፍ የምንሻገረው እንደው ወደሚቀጥዐው ምእራፍ ለመሻገር ብለን ብቻ አይደለም፡፡ ወደሚቀጥለው ምእራፍ የምንሸጋገረው የእግዚአብሄርን አላማ በሚቀጥለው ምእራፍ ውስጥ የእግዚአብሄርን አላማ ለማስፈፀም ነው፡፡ ወደ ሚቀጥለው ምእራፍ በስኬት መሸጋገር የምንችለበት አንደኛው መንገድ ያለንበትን ምእራፍ በትጋት በመጨረስ ነው፡፡ በትጋት ካልጨረስነው ያለንበት የህይወት ምእራፍ ወደሚቀጥለው ምእራፍ አይለቀንም፡፡
ስለዚህ እኔ ከሰው ሁሉ ደም ንጹሕ እንደ ሆንሁ ዛሬ በዚች ቀን እመሰክርላችኋለሁ። የእግዚአብሔርን ምክር ሁሉ ነግሬአችኋለሁና፥ ምንም አላስቀረሁባችሁም። የሐዋርያት ሥራ 20፡26-27
ያለንበት የህይወት ደረጃ ራሱ ትልቅ ግብ ነው፡፡ ስለዚህ ወደሚቀጥለው ለመሻገር እየሰራን ስለአሁኑ እግዚአብሄርን ማመስገንና የአሁኑን ማክበር ለሚመጣው እንድንታጭ ያደርገናል፡፡
እንግዲያስ በዓመፃ ገንዘብ ካልታመናችሁ፥ እውነተኛውን ገንዘብ ማን አደራ ይሰጣችኋል? በሌላ ሰው ገንዘብ ካልታመናችሁ፥ የእናንተን ማን ይሰጣችኋል? የሉቃስ ወንጌል 16፡11-12
4.     የቆየንበትን የህይወት ምእራፍ ላይ በሩን አለመጠርቀም፡፡
የነበርንበት የህይወት ምእራፍ መርገም አይደለም፡፡ የነበርንበት የህይወት ምእራፍ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ የማያስተላልፍ በር ነው፡፡ የነበርንበት የህይወት ምእራፍ ለሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ የሚያዘጋጅ የዝግጅት ጊዜ ነው፡፡ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ አለፍን ማለት ባለፈው የህይወት ምእራፍ በር ላይ ጠርቅመን እንወጣለን ማለት አይደለም፡፡ ወደሚቀጥለው የህይወት ምእራፍ በር ስንገባ ያለፈውን ምእራፍ በር ቀስ ብለን ዘግተን መውጣት አለብን፡፡ የነበርክበትን የህይወት ምእራፍ ማጣጣል የብስለት ማጣት ምልክት ነው፡፡ የነበርክበት የህይወት ምእራፍ መናቅ በአዲሱ የህይወት ምእራፍ እርግጠኛ እንዳልሆንክ የሚያሳይ የስጋት ምልክት ነው፡፡ ሰው ለዘመናት ሲጠጣበት የነበረውን ምንጭ ልክ ሊወጣ ሲል መጣላትና ውሃውነ ማደፍረስ ጤነኝነት አይደለም፡፡  
እነዚህም ጌታን ሲያመልኩና ሲጦሙ መንፈስ ቅዱስ፦ በርናባስንና ሳውልን ለጠራኋቸው ሥራ ለዩልኝ አለ። በዚያን ጊዜም ከጦሙ ከጸለዩም እጃቸውንም ከጫኑ በኋላ አሰናበቱአቸው። የሐዋርያት ሥራ 13፡2-3
5.     ያለፍንበት የህይወት ምእራፍ ሰዎችን መርዳት
እኛ ካለፈው የህይወት ምእራፍ ተሻገርን ማለት ሌሎች ሰዎች በቀድሞው ይህይወት ምእራፍ ውስጥ የሉም ማለት አይደለም፡፡ ላለፍንበት የህይወት ምእራፍ ሰዎች መራራት እና አብረናቸው መቆም የህይወትን ምእራፍ መለወጥን አስፈላጊነት በአግባቡ መረዳት ነው፡፡ ወደሚቀጥለው ምእራፍ የተሻገርነው ሌሎችን ለማሻገር እንደሆነ መርሳት የለብንም፡፡
ደግሞ የተሰጠኝን ጸጋ አውቀው፥ አዕማድ መስለው የሚታዩ ያዕቆብና ኬፋ ዮሐንስም እኛ ወደ አሕዛብ እነርሱም ወደ ተገረዙት ይሄዱ ዘንድ ለእኔና ለበርናባስ ቀኝ እጃቸውን ሰጡን፤ ድሆችን እናስብ ዘንድ ብቻ ለመኑን፥ ይህንም ደግሞ ላደርግ ተጋሁ። ወደ ገላትያ ሰዎች 2፡9-10
ከላፍንበት የህይወት ምእራፍ ሰዎች ጋር መጣላት ያሳንሰናል፡፡ ሰዎችን ባለመጣላት በመታገስ ወዳጆችን ይበልጥ እያፈራንና እያበዛን እንጂ በጥል እየቀነስን መሄድ አይገባንም፡፡
ወንድምህም ቢበድልህ፥ ሄደህ አንተና እርሱ ብቻችሁን ሆናችሁ ውቀሰው። ቢሰማህ፥ ወንድምህን ገንዘብ አደረግኸው፤ የማቴዎስ ወንጌል 18፡15
6.       በትጋትና በታማኝነት መጨረስ
ያለንበትን የህይወት ምእራፍ ለመረዳት ራሳችንን መስጠት ጥበብ ነው፡፡ ያለንበት አዲሱ የህይወት ምእራፍ አዲስ እድል እንጂ በራሱ ውጤት እንዳልሆነ አውቀን በትጋትና በታማኝነት ሩጫችንን መጨረስ ይጠበቅብናል፡፡
መልካሙን ገድል ተጋድዬአለሁ፥ ሩጫውን ጨርሼአለሁ፥ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ፤ 2ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 4፡7
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ጌታ #ኢየሱስ #ትጋት #ታማኝነት #ጊዜ #ፅናት #መጠበቅ #ምስጋና ##ሃሳብ #ቃል #እግዚአብሄር #ትጋት #መንፈስቅዱስ #ንስሃ #መለወጥ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #መጨረስ #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

No comments:

Post a Comment