Popular Posts

Friday, October 4, 2019

ከፍርሃት ነፃ የሚያወጣ ፍርሃት



ሰው ከፈጠረው ከእግዚአብሄር ጋር እንዴት መኖር እንዳለበት ካወቀ ይሳካለታል፡፡ ሰው ለፈጠረው ለእግዚአብሄር እውቅና ካልሰጠ ይወድቃል፡፡ ሰው ከፈጠረው ከእግዚአብሄር ጋር እንዴት መኖር እንዳለበት ካላወቀ ከሌላ ከምንም ነገር ጋር እንዴት መኖር እንዳለበት ቢያውቅም ዋጋ የለውም፡፡  
ሰማይና ምድርን ሰውን የፈጠረው እግዚአብሄር ነው፡፡ ሰው ከምድር ባለቤት ከእግዚአብሄር ጋር እንዴት እንደሚኖር ካላወቀ ሌሎች ሁሉ እውቀቶች ቢኖሩትም ዋናውን እውቀት አጥቶታልና ሊሳካለት አይችልም፡፡
የጥበብ ሁሉ መጀመሪያ እግዚአብሄርን መፍራት ነው፡፡ የጥበብ መሰረታዊ ፍላጎት እግዚአብሄርን መፍራት ነው፡፡ ሰው ሌላ ምንም ጥበብ ባይኖረውና እግዚአብሄርን የመፍራት ጥበብ ብቻ ካለው በምድር ላይ ነገሮችን ሁሉ ተቋቁሞ ማለፍ ይችላል፡፡ ሰው ሌሎች ጥበቦች ሁሉ ኖሮት እግዚአብሄርን የመፍራት ጥበብ ከጎደለው ይወድቃል፡፡
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ሰነፎች ግን ጥበብንና ተግሣጽን ይንቃሉ። መጽሐፈ ምሳሌ 1፡7
የጥበብ መሰረታዊ ፍላጎት ከምድር ባለቤት ጋር እንዴት መኖር እንዳለብህ ማወቅ ነው፡፡
ሰው እንዲያመልክ እና እንዲፈራ ተፈጥሮአል፡፡ ሰው እግዚአብሄርን እንዲያመልከና እንዲፈራ ተፈጥሮአል፡፡
ሰው ከእግዚአብሄር ክብር ከመውደቁ በፊት እግዚአብሄርን ብቻ በሚያመልክበትና በሚፈራበት ጊዜ ሁሉ ማንንም አይፈራም ማንንም አያመልክም ነበር፡፡
ሰው እግዚአብሄርን መፍራትና እግዚአብሄርን ማምለክ ሲያቆም ነገሮች ሁሉ ያስፈሩት ጀመሩ፡፡ ሰው እግዚአብሄርን መታዘዝ ሲያቆም በእግዚአብሄር ፍርሃት ምትክ ሌሎች ፍርሃቶች ህይወቱን ተቆጣሩት፡፡ ሰው እግዚአብሄርን ከመፍራት ሲመለስ የሌሎች ፍርሃቶች ሁሉ አስረኛ ሆነ፡፡
ሰው ወደተፈጠረበት የጥንቱ የቀደመው አላማ ሲመለስ እና የሚያስፈራው እግዚአብሄር ብቻ ሲሆን ሌሎች ፍርሃቶች ሁሉ ስፍራቸውን ይለቃሉ፡፡
ሰው እግዚአብሄርን የመፍራት ጥበብ ካለው ሌላ ምንም ነገር ሊያስፈራው አይችልም፡፡ ሰው እግዚአብሄርን የመፍራት ጥበብ ሲበዛለት ሌሎች ፍርሃቶች ሁሉ ከህይወቱ እየጠፉ ይሄዳሉ፡፡
ሰው እግዚአብሄርን ካልፈራ በምትኩ ሰይጣንን ፣ ወደፊቱን ፣ ራሱን ፣ ሁኔታን ፣ ሌሎችን ሰዎችና ነገርን ይፈራል፡፡ የሰው ልብ በእግዚአብሄር ፍርሃት ከተሞላ ሰው ከሰው ከሁኔታ እና ከነገ ፍርሃት ነፃ ይሆናል፡፡  
ሰው በአንድ ጊዜ ሁለት ነገርን ሊፈራና ሊያመልክ አይችልም፡፡
እግዚአብሄርን የሚፈራ ሰው ሌላ ምንም ነገር እስከማይፈራ ድረስ ይጠበቃል በነፃነትም ይኖራል፡፡
ሰው እግዚአብሄርን ሲፈራ ሰይጣንን አይፈራም
ሰው ፍርሃቱን ለእግዚአብሄር ከሰጠ ሰይጣን በሰው ውስጥ ምንም ፍርሃት አያገኝም፡፡ ሰው እግዚአብሄርን ከፈራ ሰይጣንን አይፈራም፡፡ ሰው ከሰይጣን እጅግ ከፍ ያውን እግዚአብሄርን ከፈራ ያነሰውን ሰይጣንን ሊፈራ አቅም ያነሰዋል፡፡
በጨለማ ከሚሄድ ክፉ ነገር፥ ከአደጋና ከቀትር ጋኔን አትፈራም። መዝሙረ ዳዊት 91፡6
አለቅነትንና ሥልጣናትን ገፎ፥ ድል በመንሣት በእርሱ እያዞራቸው በግልጥ አሳያቸው። ወደ ቆላስይስ ሰዎች 2፡15
ሰው እግዚአብሄርን ከፈራ ነገን አይፈራም
ሰው እግዚአብሄርን ከፈራ ስለዘላሙ አይፈራም፡፡ ስለዘላለሙ እርግጠኛ የማይሆነው እግዚአብሄርን በሚገባ የማይፈራ ሰው ብቻ ነው፡፡ ስለሞት የሚፈራው እግዚአብሄርን የማይፈራ ሰው ነው፡፡ እግዚአብሄርን ለሚፈራና ለሚያመልክ ሰው ሞት ከምድር ወደሰማይ ህይወት መሸጋገሪያ በር ብቻ ነው፡፡
እንግዲህ ልጆቹ በሥጋና በደም ስለሚካፈሉ፥ እርሱ ደግሞ በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን በሞት እንዲሽር፥ ይኸውም ዲያብሎስ ነው፥ በሕይወታቸውም ሁሉ ስለ ሞት ፍርሃት በባርነት ይታሰሩ የነበሩትን ሁሉ ነጻ እንዲያወጣ፥ በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ። ወደ ዕብራውያን 2፡14-15
ሰው እግዚአብሄርን ሲፈራ እና እግዚአብሄርን በመፍራት ሲያድግ ሁኔታዎችን መፍራቱ እየቀነሰና እየሞተ ይሄዳል፡፡ ሰው ሁኔታን የሚፈራው እግዚአብሄርን እንደሚገባው ስለማይፈራ ነው፡፡ ሰው ሁኔታን የሚፈራው ለእግዚአብሄር አምላክነት እውቅና ባልሰጠበት የህይወት ክፍሉ ብቻ ነው፡፡
በእሾህ መካከል የተዘራውም ይህ ቃሉን የሚሰማ ነው፥ የዚህም ዓለም አሳብና የባለጠግነት መታለል ቃሉን ያንቃል፥ የማያፈራም ይሆናል። የማቴዎስ ወንጌል 1322
ሰው ለእግዚአብሄር አምላክነት እውቅና ሲሰጥና እግዚአብሄርን እንደሚገባው ሲፈራ ሌላውን ሰው አይፈራም፡፡ ሰው ለእግዚአብሄር የሚገባውን ክብር ከሰጠ ለሌላ ሰው ክብርን ለመስጠት ምንም ቦታ አይቀረውም፡፡ ሰው እግዚአብሄርን እንደሚገባው ከፈራ ሰውን መፍራት ያቅተዋል፡፡ እግዚአብሄርን በሚገባ የሚፈራ ሰው ሌላ ሰው ለመፍራት በልቡ ቦታ አይቀረውም፡፡
ዳሩ ግን ጌታን እርሱም ክርስቶስ በልባችሁ ቀድሱት። 1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 3፡15
እግዚአብሄርን ፈርተህ ኢየሱስ ጌታ ነው ስትል ጌታ የሆኑብህ ነገሮች ሁሉ ስፍራ ይለቃሉ፡፡ እውነተኛውን ጌታ በላይህ ላይ ስትሾም ጌታ ተብዬዎቹ ሁሉ ስፍራቸውን ይለቃሉ፡፡
ኢየሱስ ጌታ እንደ ሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው በልብህ ብታምን ትድናለህና፤ ወደ ሮሜ ሰዎች 10፡9
ሰውን መፍራት ወጥመድ ነው፡፡ ሰው ከሰው ፍርሃት ባርነት የሚያመልጥበት ብቸኛው መንገድ እግዚአብሄርን ሲፈራ ነው፡፡
ሰውን መፍራት ወጥመድ ያመጣል፤ በእግዚአብሔር የሚታመን ግን እርሱ ይጠበቃል። መጽሐፈ ምሳሌ 29፡25
ሰው ለእግዚአብሄር የሚገባውን ስፍራ በህይወቱ ከሰጠ ወደፊቱ አያስፈራውም፡፡ ሰው ግን እግዚአብሄርን እንደሚገባው ካልፈራና ከእግዚአብሄርን የሚደብቀውና የሚሰስተው ነገር ሲኖር ነገን ይፈራል፡፡ ሰው ለእግዚአብሄር ክብርን በመስጠት ነፍሱን ሲተው ያገኘዋል፡፡ ሰው እግዚአብሄርን ባለመፍራት ነፍሱን አልተውም ሲል ነፍሱን በፍርሃት ያጣታል፡፡
ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል፤ ስለ እኔ ግን ነፍሱን የሚያጠፋ ሁሉ ያገኛታል። የማቴዎስ ወንጌል 16፡25
ነፍሱን የሚያገኝ ያጠፋታል፥ ነፍሱንም ስለ እኔ የሚያጠፋ ያገኛታል። የማቴዎስ ወንጌል 10፡39
እግዚአብሄርን መፍራት ውድቀትን ከመፍራት ነፃ ያወጣል
እግዚአብሄርን የሚፈራ ሰው ውድቀትን አይደፈራም፡፡ እግዚአብሄርን የሚፈራ ሰው የሚኖረው በእግዚአብሄር ምህረት ነው፡፡ እግዚአብሄርን የሚፈራ ሰው ቢሳሳት እንኳን እግዚአብሄር እንደማይጥለው ያውቃል፡፡ እግዚአብሄርን የሚፈራ ሰው እንደገና እንደሚነሳ ያውቃል፡፡
ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? ወደ ሮሜ ሰዎች 8፡35
እግዚአብሔርን መፍራት ወደ ሕይወት ይመራል፤ የሚፈራውም ጠግቦ ይኖራል፥ ክፉ ነገርም አያገኘውም። መጽሐፈ ምሳሌ 19፡23
ለእናንተ የማስባትን አሳብ እኔ አውቃለሁ፤ ፍጻሜና ተስፋ እሰጣችሁ ዘንድ የሰላም አሳብ ነው እንጂ የክፉ ነገር አይደለም። ትንቢተ ኤርምያስ 29፡11
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #ሃሳብ #ጥበብ #ማስተዋል #እግዚአብሔርንመፍራት #ጥበብ #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ  #እምነት #ቃል  #ማደስ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment