Popular Posts

Friday, December 14, 2018

ወርቃማ እድል


እግዚአብሄር እጅግ መልካም አጋጣሚዎችን ይሰጠናል፡፡ ህይወት በመልካም አጋጣሚዎች የተሞላች ነች፡፡ አይኖቻችን ተከፍተው በዙሪያችን ያሉትን መልካም አጋጣሚዎች ብንመለከት ሁልጊዜ እግዚአብሄርን በማመስገን አጋጣዎቹን ሁሉ ለእግዚአብሄር ክብር እንጠቀምባቸዋለን፡፡ 
ደስ ለመሰኘት ወርቃማ እድል
ሰው እንደ ነቢያትና እንደ እግዚአብሄር ሰው ሲሰደድ እንደ እግዚአብሄር ሰው ለመሰደድ የተገባው ተደርጎ በእግዚአብሄር ስለተቆጠረ ይህንን ወርቃማ እድል ተጠቅሞ ደስ ሊለው ይገባል፡፡
ሲነቅፉአችሁና ሲያሳድዱአችሁ በእኔም ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲናገሩባችሁ ብፁዓን ናችሁ። ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ፥ ሐሴትም አድርጉ፤ ከእናንተ በፊት የነበሩትን ነቢያትን እንዲሁ አሳድደዋቸዋልና። የማቴዎስ ወንጌል 5፡11-12
ሐዋርያትንም ወደ እነርሱ ጠርተው ገረፉአቸው፥ በኢየሱስም ስም እንዳይናገሩ አዝዘው ፈቱአቸው። እነርሱም ስለ ስሙ ይናቁ ዘንድ የተገባቸው ሆነው ስለ ተቈጠሩ ከሸንጎው ፊት ደስ እያላቸው ወጡ፤ የሐዋርያት ሥራ 5፡40-41
እግዚአብሄርን የማመስገን ወርቃማ እድል
እግዚአብሄርን ማመሰገን መስዋእትነትን ይጠይቃል፡፡ ስሜታችን ተለዋዋጭ ነው፡፡ ሁልጊዜ እግዚአብሄርን ማመስገን አይሰማንም፡፡ አንዳንዴ እግዚአብሄር ላይ ለማጉረምረም እንፈተናለን፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከማመስገን ይልቅ ማጉረምረም ይቀለናል፡፡ የምስጋና መስዋእት የሚባለው ነገሮች ሁሉ እንዳናመሰግን ሲናገሩን ሳንሰማቸው እግዚአብሄርን የምናመሰግነው ምስጋና ነው፡፡
በመልካም ጊዜ ሁሉ ሰው ያመሰግናል፡፡ በብዙ ሰዎች ዘንድ የማይገኘው ውዱ ምስጋና እግዚአብሄርን ላለማመስግን ስንፈተን ፈተናውን ተቋቁምን የምናመሰግነው ምስጋና ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚፈልገው የምስጋና መስዋእት ማጉረምረም ሲያምረን ሃሳባችንን ለውጠን እግዚአብሄርን የምናመሰግነውን ምስጋና ነው፡፡
ለእግዚአብሔር የምስጋናን መሥዋዕት ሠዋ፥ ለልዑልም ስእለትህን ስጥ፤ መዝሙረ ዳዊት 50፡14
ራስን ለማዋረድ ወርቃማ እድል
ስጋዊ ባህሪያችን መዋረድን አይፈልግም፡፡ ስጋዊ ባህሪያችን የራሱ የሆነ ክብር አለው፡፡ ስጋዊ የሃጢያተኛ ባህሪያችን ራሱን ከፍ ከፍ ለማድረግ እንጂ ራሱ ለማዋረድ ቦታ የለውም፡፡ ስጋችንን የሚያዋርድ ነገር ሲያጋጥምን አለመቃወም ስጋችን እንዲዋረድ የቀረበልንን ወርቃማ እድል በአግባቡ መጠቀም ነው፡፡ ስጋችንን የሚያዋርድ ክፉ ሲያጋጥመን ክፉውን ባለመቃወም እንዲጎሸም ስጋችን ላይ መፍረድ ይገባናል፡፡   
እኔ ግን እላችኋለሁ፥ ክፉውን አትቃወሙ፤ ዳሩ ግን ቀኝ ጉንጭህን በጥፊ ለሚመታህ ሁሉ ሁለተኛውን ደግሞ አዙርለት፤ የማቴዎስ ወንጌል 5፡39
ነገር ግን ለሌሎች ከሰበክሁ በኋላ ራሴ የተጣልሁ እንዳልሆን ሥጋዬን እየጎሰምሁ አስገዛዋለሁ። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 9፡27
ህሊናን የመንካት ወርቃማ እድል
በተፈጥሮአዊው ሰው የተለመደው ክፉ ለሚያደርግ ክፉ ማድረግ ነው፡፡ ሰውን በክፉ ማሸነፍ የስጋ ልምድ ነው፡፡ ሰው እልክ ውስጥ ከገባ ህሊናውን አይሰማም፡፡ ክፉ ለሚያደርግ ግን መልካም ማድረግ በዚህ አለም ያልተለመደ እንግዳ ድርጊት ነው፡፡ ክፉን በመልካም ማሸነፍ ሰውን የሚያሳቅቅ ፣ የሚያሳፍርና ህሊናን የሚነካ ነገር ነው፡፡ ሰው ክፉ ሲያደርግ መልካምን መለስ ሰውን ማንቃትና የሰውን ህሊና መንካት ነው፡፡ 
ጠላትህ ግን ቢራብ አብላው፤ ቢጠማ አጠጣው፤ ይህን በማድረግህ በራሱ ላይ የእሳት ፍም ትከምራለህና። ክፉውን በመልካም አሸንፍ እንጂ በክፉ አትሸነፍ። ወደ ሮሜ ሰዎች 12፡20-21
በእግዚአብሄር ፀጋ ለመመካት ወርቃማ እድል
ማንም ሰው አንድ ምዕራፍ ትሄድ ዘንድ ቢያስገድድህ ሁለተኛውን ከእርሱ ጋር ሂድ። የማቴዎስ ወንጌል 5፡41 
ሰው ሁሉ ለእኔ ይገባኛል በማለት ለራሱ ሲከራከር ለሌላው ሰው መከራከር በዚህ አለም ያልተለመደ ድርጊት ነው፡፡ ሰው ሁሉ ለእና እኔ የእኔ ሲል የአንተ ለአንተ የሚል ሰው ሲገኝ ያስደነግጣል፡፡ ከሰማይ በታች ያለው ራሰ ወዳድነትና ስግብግብነት ነው፡፡ ፍቅርና ሌላወን ማገልገል ግን ከሰማይ ነው፡፡ ሰው በስጋው ራሱን ሊወድ ይችላለ፡፡ ነገር ግን ካለምክኒያት እንዲሁ ሌላውን መውደድ ከሰማይ ነው፡፡ ሰዎች ጉልበታቸውን ሲቆጥቡና ለራሳቸው ሲከራከሩ አንድ ለሚጠይቅህ ሁለት ማድረግ እኔ ከዚህ ምድር አይደለሁም ብሎ መመካት ነው፡፡ ሰው ስለ አንዱ ምእራፍ ሲያጉረመርም ሁለተኛውን መጨመር ከዚህ አለም ያልሆነ የአግዚአብሄር ሃይል በእኛ እንደሚሰራ የምናሳይበት ወርቃማ አጋጣሚ ነው፡፡ ሰው ስለአነዱ ምእራፍ ሲከራከር ሁለተኛውን መጨመር በእኛ ስለሚሰራው የእግዚአብሄ ፀጋ ሰውን ማንቆላለጭ ነው፡፡ ሰው ስለ አንዱ ምእራፍ ሲያጉረመርም ሁለተኛውን መጨመር በእኛ ስለሚሰራው የእግዚአብሄር ሃይልና ለሰዎች መመስከር ነው፡፡
ፍፁም የመሆን ወርቃማ እድል
በመከራ መታገስ ስጋዊ ባህሪያችንን ይገድላል፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ በፈተና መታገስ ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም የሚለው ስለዚህ ነው፡፡
ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም። የያዕቆብ መልእክት 1፡2-4
ሰዎችን ለመባረክ ወርቃማው እድል
እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፥ የሚረግሙአችሁንም መርቁ፥ ለሚጠሉአችሁም መልካም አድርጉ፥ ስለሚያሳድዱአችሁም ጸልዩ፤ የማቴዎስ ወንጌል 5፡44-45
አንዳንድ ሰውን ለመባረክ ትዝ ላይለን ሁሉ ይችላል፡፡ እውነት ነው እግዚአብሄር በመንፈስ ቅዱስ አስታውሶንና ወደልባችን መጥቶ ለሰዎች እንድንፀልይና እንድናባርካቸው ሊያደርገን ይችላል፡፡ ነገር ግን ሰዎች ከፉ ሲያደርጉብንና ስለእነርሱ ማሰብ ሰንጀምር ይህንን አጋጣሚ እግዚአብሄር በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረን ሰው ለመባረክ ብንጠቀምበት በረከቱ ለእኛ ነው፡፡ ሰውን ለመርገም ስንፈተን ክፉ ላደረገብን ሰው ስንፀልይ ይህንን ወርቃማ አጋጣሚ በአግባቡ ተጠቀምንበት ማለት ነው፡፡ የሰውን ክፋት ለማሰብ እንቅልፋችንን ባጣንበት ጊዜ ተጠቅመን ለዚያ ሰው ብንፀልይለትና ብንባርከው እግዚአብሄር እኛንም ይባርከናል የበደለንንም ሰው በይቅርታና በምህረትና በማስተዋል ይባርከዋል፡፡
ፍቅርን ለመለማመድ ወርቃማ እድል
ፍቅርን የምንለማመደው በመልካም ጊዜ ብቻ አይደለም፡፡ ስለሰው ፍቅር ብለን ነገሮችን መተው መልቀቅ የምማረው ሰዎች የእኛን ነገር ሲወስዱ ነው፡፡ ፍቅርን የምንለማመደው ነጣቂ ክፉ ሰው ሲኖር ነው፡፡ ፍቅርን የምንለማደው ላለመተው ስንፈተን መተው ሲያመን በመተው ነው፡፡ ፍቅርን የምንለመማደው ስጋዊ ባህሪያችን አትልቀቀው ልክ አስገባው ሲለን እምቢ ስጋችንን ዝም አሰኝተን እና ጎሽመን እንዲያውም መልካምነትን ስንጨምርለት ነው፡፡
እንዲከስህም እጀ ጠባብህንም እንዲወስድ ለሚወድ መጎናጸፊያህን ደግሞ ተውለት፤ የማቴዎስ ወንጌል 5፡40
ራሰን የማወቅ ወርቃማ እድል
ብዙ ጊዜ ለራሳችን የተሳተ ግምት ይኖረናል፡፡ ብዚ ጊዜ ራሳችንን የምናየው እግዚአብሄር ከሚያየን ያነሰ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንዴት ከፍ አድርጎ እንደሚያየን ስናይ እድሉን ተጠቅመን ደስ ሊለን ይገባል፡፡ እግዚአብሄር ይችላል ብሎ የሚያየንን ከፍ ያለ አስተያየት ስናይ እግዚአብሄርን ልናመሰግነው ይገባል፡፡ ከፍ ያለ መከራ በህይወታችን ሲመጣ የሚችሉት ነው ብሎ እግዚአብሄር ስለፈቀደ ደስ ሊለን ይገባል፡፡ እኛ እንችለውም ብለን ያሰብነው መከራ እርሱ ይችሉታል ብሎ በእኛ መተማመኑን ከማወቅ የበለጠ የሚያስደስት ነገር የለም፡፡ ከፍ ያለው የፈተና ደረጃ የእኛን የህይወት የብስለትና የእድገት ደረጃ ስለሚያሳይ ደስ ሊለን ይገባል፡፡
ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 10፡13
እግዚአብሄርን ለመምሰል ወርቃማ እድል
ሁላችን እግዚአብሄርን መምሰል እንፈልጋለን፡፡ ሁላችንም እግዚአብሄርን በሁሉ መከተል እንፈልጋለን፡፡ ሁላችንም እግዚአብሄርን በህይወታችን ማክበር እንፈልጋለን፡፡ የእግዚአብሄርን መልክ ለምድር ህዝብ የምናሳይበት ወርቃማ አጋጣሚ እንደ እግዚአብሄር ይቅር ስንልና ለጠሉን ሰዎች መልካም ስናደርግ ነው፡፡
እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፥ የሚረግሙአችሁንም መርቁ፥ ለሚጠሉአችሁም መልካም አድርጉ፥ ስለሚያሳድዱአችሁም ጸልዩ፤ እርሱ በክፎዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣልና፥ በጻድቃንና በኃጢአተኞችም ላይ ዝናቡን ያዘንባልና። የማቴዎስ ወንጌል 5፡44-45
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #መሪ #ፀጋ #የሚያስችልሃይል #መልካም #ክፉ #አሸንፍ #ብቃት #የእግዚአብሄርችሎታ #የእግዚአብሄርሃይል #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ትጋት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ፅድቅ #እግዚአብሄርንመምሰል #ራስንመግዛት #ልብ #ምስክርነት

No comments:

Post a Comment