Popular Posts

Monday, December 10, 2018

የገዛ ሚስቱን የሚወድ ራሱን ይወዳል


እንዲሁም ባሎች ደግሞ እንደ ገዛ ሥጋቸው አድርገው የገዛ ሚስቶቻቸውን ሊወዱአቸው ይገባቸዋል። የገዛ ሚስቱን የሚወድ ራሱን ይወዳል፤ ማንም የገዛ ሥጋውን የሚጠላ ከቶ የለምና፥ ነገር ግን የአካሉ ብልቶች ስለሆንን፥ ክርስቶስ ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን እንዳደረገላት፥ ይመግበዋል ይከባከበውማል። ወደ ኤፌሶን ሰዎች 5፡28-30
ሰው ለራሱ ያለው አክብሮት የሚታየው ሚስቱን በማክበር ነው፡፡ ሰው ለራሱ ያለው አክብሮት የሚፈተነው ሚስቱን በማክበሩ ላይ ነው፡፡ ራሱን የሚያከብር የሚመስለው ሚስቱን ግን የማያከብር ሰው ተታሏል፡፡ ሰው ለራሱ ያለውን አክብሮት የሚለካው ለሚስቱ ያለውን አክብሮት በማየት ነው፡፡  
ራሱን የሚቀበልና የሚወድ ሰው ሚስቱን ይቀበላል ይወዳል፡፡ ራሱን እንዳለ የሚቀበል ሰው ሚስቱን እንዳለ ይቀበላል፡፡ ራሱን የማይጠላ ሰው ሚስቱን አይጠላም፡፡
የሰው የሚስቱን ያለመውደድ ችግር ከሚስት አለመውደድ ችግር ያለፈ ነው፡፡ የሰው ሚስቱን ያለመውደድ ችግር ራስን ያለመውደድ ችግር ነው፡፡
ሰው እግዚአብሄር እንዴት እንደሚወደው የተረዳ ሰው ሚስቱን እግዚአብሄር እንዴት እንደሚወዳት ይረዳል፡፡ እርሱን እግዚአብሄር እንዴት እንደሚወደው ያልተረዳ ሰው እግዚአብሄር ሚስቱን እንዴት እንደሚወዳት ባይረዳ አይገርምም፡፡
የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና፦ ከክብሩ በኋላ ወደ በዘበዙአችሁ አሕዛብ ልኮኛል፤ የሚነካችሁ የዓይኑን ብሌን የሚነካ ነውና። ትንቢተ ዘካርያስ 2፡8
የሰው ሚስቱን ያለመውደድ ችግር የጀመረው ሚስቱን ባለመውደድ ሳይሆን ራሱን ባለመውደድ ነው፡፡ ራሱ የሚነቅ ሰው ሚስቱን ቢንቅ አይገርምም፡፡  
የሚስትን ያለመውደድ ችግር የሚፈታው ራስን በመውደድ ለራስ የሚገባውን አክብሮት እና ፍቅር በመስጠት ነው፡፡
ሰው ሌላውን የሚያየው ራሱን በሚያይበት ነፀብራቅ ነው፡፡
ሰው ራሱን ከሚወደው በላይ ሌላውን አይወድም፡፡ ሰው ሌላውን መውደድ የሚማረው ራሱን በመውደድ ተለማምዶ ነው፡፡ ሰው ራሱን ከሚወድው በላይ ሌላውን መውደድ አይችልም፡፡ ሰው ሌላውን የሚወደው ራሱን የሚወደውን ያህል ብቻ ነው፡፡  
ሁለተኛይቱም፦ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የምትል እርስዋን የምትመስል ይህች ናት። ከእነዚህ የምትበልጥ ሌላ ትእዛዝ የለችም። የማርቆስ ወንጌል 12፡31
ሰው እንዴት መወደድ እንደሚፈልግ የምንማረው በራሳችን ነው፡፡ የሰውን የመውድድ ፍላጎት የምናጠናው ራሳችንን በመሰለልና በማጥናት ነው፡፡ ሰውን የመውደድ ስነ ጥበብ የምንማረው በራሳችን ነው፡፡
ሰዎችም ሊያደርጉላችሁ እንደምትወዱ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉላቸው። የሉቃስ ወንጌል 6፡31
ሚስትን ለመውደድ ቀላሉ መንገድ ራስን መውደድ መማር ነው፡፡ ሚስትን የመውደድ አቋራጭ መንገድ ራስን በመውደድና በማክበር ፍቅርን በራስ ላይ መለማመድ ነው፡፡
እንዲሁም ባሎች ደግሞ እንደ ገዛ ሥጋቸው አድርገው የገዛ ሚስቶቻቸውን ሊወዱአቸው ይገባቸዋል። የገዛ ሚስቱን የሚወድ ራሱን ይወዳል፤ ማንም የገዛ ሥጋውን የሚጠላ ከቶ የለምና፥ ነገር ግን የአካሉ ብልቶች ስለሆንን፥ ክርስቶስ ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን እንዳደረገላት፥ ይመግበዋል ይከባከበውማል። ወደ ኤፌሶን ሰዎች 5፡28-30
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ህይወት #ጋብቻ #ትዳር #ባል #ሚስት #ፍቅር #መውደድ #ይተዋል #ይጣበቃል #አንድስጋ #እውነት #ትህትና #ትንሳኤ #ህይወት #ወንጌል #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ  #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ  

No comments:

Post a Comment