Popular Posts

Friday, February 3, 2017

ለፍቅር ተፈጥረናል

ሰውን የፈጠረው እግዚአብሄር ነው፡፡ እግዚአብሄር ደግሞ ፍቅር ነው፡፡ ሰው የተፈጠረው በፍቅር ነው፡፡ ሰው የታለመውና የታቀደው በፍቅር እንዲኖር ነው፡፡ ሰው ዲዛይን የተደረገው ለፍቅር ህይወት ነው፡፡ ሰው ከንድፉ ከፍቅር ህይወት ሲወጣ ሁሉም ነገር ይዛባበታል፡፡ ሰው በፍቅር ሲኖር ሁሉ ነገር ይሰራለታል፡፡
መኪና የተሰራው እንዲነዳ ነው፡፡ ነገር ግን መኪና ሲበላሽና ሲገፋ የተለመደ ተፈጥሮአዊ አይደለም፡፡ የምትወዱት መኪና ሲበላሽ ያስጠላችኋል፡፡ መኪናን የሰራው ሰው ከመስራቱ በፊት ሰው ውስጡ ገብቶ እንዲያስነሳውና እንዲነዳው ነው፡፡ መኪና የተሰራው እንዲነዳ ነው፡፡
የተነደፍነው የታቀድነውና የተሰራነው ለፍቅር ስለሆነ ለእኛ በፍቅር መኖር ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ በተቃራኒው ለጥላቻ ስላልተሰራን ጥላቻ እጅግ ከባድ ስራ ነው፡፡ የተሰራንበት አላማ ስለሆነ ሰውን ለመውደድ በብርሃን እናደርገዋለን፡፡ ሰውን ለመጥላት ግን ተፈጥሮአችን ስላይደለ ሰው እንዳያውቅብን ስለምንጠነቀቅ በፍቅር የምንኖር እያስመሰልን ስለሆነ በጣም ከባድ ስራ ነው፡፡ በፍቅር መኖር ህይወታችንን ቀለል ሲያደርገው በጥላቻ መኖር ህይወታችንን እጅግ ያወሳስበዋል፡፡
ሰው የተሰራው ለፍቅር ነው፡ ሰው በፍቅር ሲኖር ያምረበታል፡፡ ሰው በጥላቻ ሲኖር ክብሩን ያጣል፡፡ ሰው በፍቅር ሲኖር ጤናውን ይጠበቃል ሰው በጥላቻ ሲኖር ጤናውን ያጣል፡፡
ሰው በፍቅር ሲኖር ብቻ ነው እውነተኛ ስኬት ውስጥ የሚገባው፡፡ ሰው በፍቅር ሲኖር ብቻ ነው የሚረካው፡፡ ሰው በፍቅር ሲኖር ብቻ ነው የሚገባውን ኑሮ የሚኖረው፡፡ 1ቆሮንጦስ 13፡4-8
የፍቅር ህይወት አስተማማኝ ህይወት ነው፡፡ ስለዚህ ነው መፅሃፍ ቅዱስ በፍቅር ላይ የሚሰራ ምንም ህግ እንደሌለ ያስተምራል፡፡ ሰው በፍቅር ኖሮ አይሳሳትም፡፡ ፍቅር የሚወጣለት ነገር የለም፡፡ ሰው ለሰው መልካም አስቦ ፣ ስለሰው መልካም ተናግሮና ስለሰው መልካም አድርጎ አይስትም፡፡
የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፥ የውሃት፥ ራስን መግዛት ነው። እንደዚህ ያሉትን የሚከለክል ሕግ የለም። ገላትያ 5፡22-23
ፍቅር ሌላውን በመረዳት ከሌላው ጋር ራስን ማስተባበር ነው፡፡
የእግዚአብሄር ትእዛዝ እንኳን ውደድ በሚለው አንድ ቃል ይጠቃለላል፡፡ ሰው በፍቅር ከኖረ የእግዚአብሄርን ህግ ሁሉ ፈፅሞታል፡፡ ሰው እግዚአብሄርን ከወደደና ሰውን ከወደደ የእግዚአብሄርን ከሰው የሚፈልገውን ፍላጎት ሁሉ አሟልቷል፡፡
በፍጹም ልብ በፍጹም አእምሮም በፍጹም ነፍስም በፍጹም ኃይልም እርሱን መውደድ፥ ባልንጀራንም እንደ ራስ መውደድ በሙሉ ከሚቃጠል መሥዋዕትና ከሌላው መሥዋዕት ሁሉ የሚበልጥ ነው አለው። ማርቆስ 12፡33
ሕግ ሁሉ በአንድ ቃል ይፈጸማልና፥ እርሱም፦ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የሚል ነው። ገላትያ 5፡14
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ፍቅር #የህግፍፃሜ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ዲዛይን #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ንድፍ #መንፈስቅዱስ #እቅድ #ልብ #መሪ

No comments:

Post a Comment