Popular Posts

Tuesday, September 20, 2016

አካባቢያችንን እንጠብቅ

ሰው አካባቢውን ከአየርና ከውሃ ብክለት ለመጠበቅ ታላቅ እንቅስቃሴ ይደረጋል፡፡ ሰዎች የአለምን አረንጓዴነትና ለጤና ተስማሚነት ለመጠበቅ ማንኛውም ነገር ያደርጋሉ፡፡
ምድርን የሚበክልን ነገር ለምሳሌ የከታላላቅ ፋብሪካዎች የሚወጣውን የተበከለ ጭስ እንዲቀነስ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ያደርጋሉ፡፡ ምክኒያቱም በቀጣይነት በቆሻሻ አካባቢ ውስጥ የሚኖር ሰው ከመታመምና ከመሞት ሊያመልጥ አይችልም፡፡
ከዚህ ሁሉ በላይ ግን አለማችንን የሚበክለው እግዚአብሄርን ባለማመንና ጥርጣሬ ነው፡፡ ሰው አካባቢውን በእግዚአብሄር ቃል ካልሞላ እግዚአብሄርን ካላመነ በስተቀር እግዚአብሄርን ደስ ሊያሰኝ ከእግዚአብሄር የሆነውንም ነገር ሊቀበል አይችልም፡፡ ከባቢው ተበላሽቶ እግዚአብሄርን ማመን ካቃተው ሰው የሚበልጥ ምስኪን ሰው የለም፡፡
ሰይጣን የሚመጣው ሊሰርቅ ሊያርድ ሊያጠፋ ነው፡፡ ሰይጣን የአስተሳሰብ አካባቢያችንን በመበከል መንፈሳዊ ጤንነታችንን የሚጎዱ ነገሮችን ሊያስፋፋ ይመጣል፡፡
የሰይጣን የመስረቂያ የማረጃና የማጥፊያ አካባቢዎች አለማመን ፍርሃትና ጥርጣሬ ናቸው፡፡
ስለዚህ ነው መፅሃፍ ቅዱስ አካባቢያችንን በእግዚአብሄር ቃል እንድንሞላና ንፅህናውን ከአለማመን እንድንጠብቅ የሚያስተምረን፡፡ አካባቢያችን በእግዚአብሄር ቃል ስንሞላና የእግዚአብሄርን ቃል ስንሰማ ንፁህ መንፈሳዊ አየርን መተንፈስ እንችላለን፡፡
የእስራኤል ህዝብ እግዚአብሔርን በፍጹም ልብ በፍጹምም ነፍስ በፍጹምም ኃይል ለመውደድ አካባቢያቸውን በእግዚአብሄር ቃል እንዲሞሉና ከብክለት እንዲጠብቁና እንዲያፀዱ ተመክረዋል፡፡
አንተም አምላክህን እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ በፍጹምም ነፍስህ በፍጹምም ኃይልህ ውደድ። እኔም ዛሬ አንተን የማዝዘውን ይህን ቃል በልብህ ያዝ። ለልጆችህም አስተምረው፥ በቤትህም ስትቀመጥ፥ በመንገድም ስትሄድ፥ ስትተኛም፥ ስትነሣም ተጫወተው። በእጅህም ምልክት አድርገህ እሰረው፤ በዓይኖችህም መካከል እንደክታብ ይሁንልህ። በቤትህም መቃኖች በደጃፍህም በሮች ላይ ጻፈው። ዘዳግም 6፡5-9
የእግዚአብሄር ህዝብ መሪ የነበረው ኢያሱ የእግዚአብሄርን ቃል ለመፈፀም እንዲያስችለው ቃሉን በቀንና በሌሊት እንዲያሰላስልና በቃሉ አካባቢ ውስጥ እንዲኖር ታዟል፡፡
የዚህ ሕግ መጽሐፍ ከአፍህ አይለይ፥ ነገር ግን የተጻፈበትን ሁሉ ትጠብቅና ታደርግ ዘንድ በቀንም በሌሊትም አስበው፤ የዚያን ጊዜም መንገድህ ይቀናልሃል ይከናወንልሃልም። እያሱ 1፡8
እግዚአብሄር እንደልቤ ያለው መዝሙረኛው ዳዊት መዝሙሩን የጀመረው አካባቢውን ከክፋት ሃሳብ ብክለት ስለሚጠብቅና በእግዚአብሄር ቃል ከባቢ ውስጥ ስለሚኖረው ሰው ምስጉንነትና የዘወትር ክንውን በመናገር ነው፡፡
ምስጉን ነው በክፉዎች ምክር ያልሄደ፥ በኃጢአተኞችም መንገድ ያልቆመ፥ በዋዘኞችም ወንበር ያልተቀመጠ። ነገር ግን በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለዋል፥ ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያስባል። እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፤ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል። መዝሙር 1፡1-3
ሃዋሪያው ሰው አለምን የማይመስልበትን ብቸኛው መንገድ የሃሳብን አካባቢ በእግዚአብሄር ቃል በማፅዳትና በመጠበቅ እንደሆነ ያስተምራል፡፡
የእግዚአብሔር ፈቃድ እርሱም በጎና ደስ የሚያሰኝ ፍጹምም የሆነው ነገር ምን እንደ ሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ። ሮሜ 12፡2
መንፈሳዊ ህይወታችንን ከብክለት ለመጠበቅ በአስተሳሰብ አካባቢያችን የሚፈቀድላቸውና የማይፈቀድላቸው ነገሮች ሊኖሩ እንደሚገቡ መፅሃፍ ቅዱስ በአፅንኦት ያስተምራል፡፡
በቀረውስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ እውነተኛ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ጭምትነት ያለበትን ነገር ሁሉ፥ ጽድቅ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ንጹሕ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ፍቅር ያለበትን ነገር ሁሉ፥ መልካም ወሬ ያለበትን ነገር ሁሉ፥ በጎነት ቢሆን ምስጋናም ቢሆን፥ እነዚህን አስቡ፤ ፊሊጲስዮስ 4፡8
ስለዚህ ነው ኢየሱስ ደቀመዛሙርቱን ምን እንደምትሰሙ ተጠበቁ ያላቸው፡፡
አላቸውም፦ ምን እንድትሰሙ ተጠበቁ። ማርቆስ 4፡24
ስለዚህ ነው የእግዚአበሄር ቃል በቤታችን በስልኮቻችን በመኪናችን ልንሰማና ልናነብ የሚገባን፡፡ ለዚህ ነው ባገኘነው አጋጣሚ የእግዚአብሄርን ቃል ከባቢ መፍጠር ያለብን፡፡ ለዚህ ነው የእግዚአብሄርን ቃል ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ መጫወት ያለብን፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል ለመስማት ለመረዳትና ለመጠበቅ የእግዚአብሄርን ቃል አካባቢ መፍጠርና በከባቢው ውስጥ መኖር አለብን፡፡ ስለዚህ ነው መፅሃፍ ቅዱስ አጥብቀህ አካባቢህን ጠብቅ ያለው፡፡
ልጄ ሆይ፥ ንግግሬን አድምጥ ወደ ቃሌም ጆሮህን አዘንብል። ከዓይንህ አታርቃት፥ በልብህም ውስጥ ጠብቃት። ለሚያገኙአት ሕይወት፥ ለሥጋቸውም ሁሉ ፈውስ ነውና። አጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፥ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና። ምሳሌ 4፡20 ፣ 22-23
አንተም አምላክህን እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ በፍጹምም ነፍስህ በፍጹምም ኃይልህ ውደድ። እኔም ዛሬ አንተን የማዝዘውን ይህን ቃል በልብህ ያዝ። ለልጆችህም አስተምረው፥ በቤትህም ስትቀመጥ፥ በመንገድም ስትሄድ፥ ስትተኛም፥ ስትነሣም ተጫወተው። በእጅህም ምልክት አድርገህ እሰረው፤ በዓይኖችህም መካከል እንደክታብ ይሁንልህ። በቤትህም መቃኖች በደጃፍህም በሮች ላይ ጻፈው። ዘዳግም 6፡5-9
ይህንን ፅሁፍ ሼር ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes

No comments:

Post a Comment