Popular Posts

Monday, May 15, 2023

ጌታ ይገሥጽህ

 

ሰይጣንን ጌታ ይገስፀው የሚለውን ንግግር ተደጋግሞ እንሰማለን፡፡ ጌታ ይገስፀው የሚለውን ንግግር ከመጠቀማችን በፊት መፅሃፍ ቅዱሳዊ ነው ወይስ የተሳት ነገር ግን ተለምዶ አነጋገር ነው የሚለውን ከእግዚአብሄር ቃል ማየት ይገባናል፡፡ ንግግሩ ከትልቅ እስከ ትንሽ በብዙዎች ዘንድ የተለመደ ንግግር ነው፡፡ በእግዚአብሄር ቃል አስተምሮት ካልተደገፈ በስተቀር ንግግሩ የተለመደ መሆኑ ብቻ ከመቀፅበት መፅሃፍ ቅዱሳዊ አያደርገውም፡፡

እውነት ነው ከእግዚአብሄ የተለያየን ሃጢያተኞች በነበርን ጊዜ እና ጌታን በማናውቅበት ጊዜ ከሰይጣን ስልጣን በታች ነበርን፡፡

በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችሁ፤ በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው። ወደ ኤፌሶን ሰዎች 2፡1-2

ክርስቶስን ስንቀበል ግን ክርስቶስ በመስቀል ላይ ድል በነሳው በሰይጣን ኃይል ላይ ሁሉ ላይ ስልጣን ተሰጥቶናል፡፡

ሰብዓውም በደስታ ተመልሰው፦ ጌታ ሆይ፥ አጋንንት ስንኳ በስምህ ተገዝተውልናል አሉት። እንዲህም አላቸው ሰይጣንን እንደ መብረቅ ከሰማይ ሲወድቅ አየሁ። እነሆ፥ እባቡንና ጊንጡን ትረግጡ ዘንድ፥ በጠላትም ኃይል ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጥቻችኋለሁ፥ የሚጐዳችሁም ምንም የለም። የሉቃስ ወንጌል 10፡17-19

መፅሃፍ ቅዱስ ሰይጣንን የመገሰፅ ሃላፊነትን የሰጠው በክርስቶስ ኢየሱስ ዳግመኛ ለተወለድን ለእኛ ለእግዚአብሄር ልጆች ነው፡፡

ኢየሱስም ቀረበና እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፦ ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ። እንግዲህ ሂዱና ...

ክርስቶስ በመስቀል ላይ በከፈለው የሃጢያው ዋጋ የሰይጣንን ስልጣን ገፎታል፡፡

አለቅነትንና ሥልጣናትን ገፎ፥ ድል በመንሣት በእርሱ እያዞራቸው በግልጥ አሳያቸው። ወደ ቆላስይስ ሰዎች 2፡10

የማቴዎስ ወንጌል 28፡18-20

ክርስቶስ ኢየሱስን እንደአዳኛችን የተቀበልን ሁላችን ፀንተን እንድንቆም ዲያቢሎስን እንድንቃወም ተሰጥቶናል፡፡

የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ። ወደ ኤፌሶን ሰዎች 6፡11

ጌታ ይገስፀው የሚለው ንግግር የመጣው መላኩ ሚካኤል ከዲያቢሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ከተናገረው የመፅሃፍ ቅዱስ ጥቅስ ውስጥ ተወስዶ ነው፡፡

የመላእክት አለቃ ሚካኤል ግን ከዲያብሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለ ሙሴ ሥጋ ሲነጋገር፦ ጌታ ይገሥጽህ አለው እንጂ የስድብን ፍርድ ሊናገረው አልደፈረም። የይሁዳ መልእክት 1፡9

ለእኛ የእግዚአብሄ ልጅነት ለተሰጠን ግን በዲያቢሎስ ላይ ስልጣን ተሰጥቶናል፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ ዲያቢሎስን ተቃወሙት ገስፁት አስወጡት በሚሉ ትምህርቶች የተሞላ ነው፡፡ ከላይ ከተጠቀሰው የመላእክ ንግግር ውጭ በተለይ በአዲስ ኪዳን  ጌታ ይገስፀው የሚለው ንግግር አይቼ አላውቅም፡፡ በኢየሱስም ንግግር ይሁን  የትኛውም ሃዋርያ ወይም የአዲስ ኪዳን መልእክት ፀሃፊ በአዲስ ኪዳን መልእክቶች ውስጥ ጌታ ይገስፀው ብሎ ሲናገር ወይም ጌታ ይገስፀው በሉ ብሎ ሲያስተምር አላነበብኩም፡፡

ዲያቢሎስን ጌታ ይገስፀው ማለት ዲያቢሎስን ተቃወሙት የሚለው የመፅሃፍ ቅዱስ ሃላፊነት አለመወጣት ነው፡፡  ዲያቢሎስን ጌታ ይገስፀው ማለት ገስፁት ብሎ አስቀድሞ ሃላፊነትን ለሰጠን ለእግዚአብሄር እንደገና መልሶ ማስተላለፍ ነው፡፡

ካልተጠነቀቅን እግዚአብሄር የሰይጣንን ስልጣን ገፎ ስልጣኑን ለእኛ ሰጥቶ ገስፁት እያለ እኛ ደግሞ ጌታ ይገስፀው እያልን "ገስፀው ገስፀው" እየተባባልን በመሃል ቤት ዲያቢሎስ ሳይገሰፅ ሊቀር ነው፡፡

ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና፤በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት።1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 5፡8-9

እንግዲህ ጌታ ይገስፀው የሚለውን ባዶ የሃይማኖት መልክ ንግግር ትተን ዲያቢሎስን ፀንታችሁ ተቃወሙት የሚለውን የእግዚአብሄን ቃል ትእዛዝ እንታዘዝ፡፡

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa


No comments:

Post a Comment