Popular Posts

Sunday, May 14, 2023

የሕይወት መውጫ ልብህን አጥብቀህ ጠብቀው


አጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፥ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና። መጽሐፈ ምሳሌ 4:23

ልብ የህይወት ቁልፍ ስፍራ ነው፡፡ ልብ ከተበላሸ ህይወት ይበላሻል፡፡ ልብ ጤነኛ ከሆነ ህይወት ጤነኛ ይሆናል፡፡

እኛ ሰዎች ግን ብዙ ጊዜ የውስጡን ልብ ላይ አናተኩርም ይልቁንም የምናየው ውጪኛውን ፊትን ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚያየው ደግሞ ልብን ነው፡፡

እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን፦ ፊቱን የቁመቱንም ዘለግታ አትይ፤ ሰው እንዲያይ እግዚአብሔር አያይምና ናቅሁት፤ ሰው ፊትን ያያል፥ እግዚአብሔር ግን ልብን ያያል አለው። መጽሐፈ ሳሙኤል ቀዳማዊ 16፡7

እንደሰው ብዙ ጊዜ የምንጨነቀው ፣ የምንጣላው እና የምንጨቃጨቀው ስለውጭኛው ልብስ ነው፡፡

ከልብ ክፉ አሳብ፥ መግደል፥ ምንዝርነት፥ ዝሙት፥ መስረቅ፥ በውሸት መመስከር፥ ስድብ ይወጣልና። የማቴዎስ ወንጌል 15፡19

ብዙ ጊዜ ማስተካከል የምንፈልገው የውጭው ንግግራችንን ነው፡፡ ነገር ግን ህይወታችን በእውነት መስተካከል ካለበት የሚስተካከለው ከልብ ጀምሮ ነው፡፡ ከልብ ያልጀመረ ለውጥ የውሸት ለውጥ ነው፡፡

እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፥ በውስጡ ቅሚያና ስስት ሞልቶ ሳለ የጽዋውንና የወጭቱን ውጭ ስለምታጠሩ፥ ወዮላችሁ። አንተ ዕውር ፈሪሳዊ፥ ውጭው ደግሞ ጥሩ እንዲሆን አስቀድመህ የጽዋውንና የወጭቱን ውስጡን አጥራ። እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፥ በውጭ አምረው የሚታዩ በውስጡ ግን የሙታን አጥንት ርኩሰትም ሁሉ የተሞሉ በኖራ የተለሰኑ መቃብሮችን ስለምትመስሉ፥ ወዮላችሁ። እንዲሁ እናንተ ደግሞ በውጭ ለሰው እንደ ጻድቃን ትታያላችሁ፥ በውስጣችሁ ግን ግብዝነትና ዓመፀኝነት ሞልቶባችኋል። የማቴዎስ ወንጌል 23፡25-28

መፅሃፍ ቅዱስ ልብህን አጥብቀህ ጠብቅ የሚለው ለዚህ ነው፡፡

ልባችን በ"ክፉ አሳብ፥ መግደል፥ ምንዝርነት፥ ዝሙት፥ መስረቅ፥ በውሸት መመስከር፥ ስድብ" እንዳይበከል እና መላው ህይወታችንን እንዳይበክል በከፍተኛ ትጋት ልባችንን ልንጠብቅ ይገባል፡፡

የልባችን በጥላቻ እና በምሬት መቆሸሽ እንደሚጎዳን የትኛውም ውዱ ወርቅና ብራችን መጥፋት አይጎዳንም፡፡ የወርቅ እና የብራችን መጥፋት እንደልብ መቆሸሽ ህይወታችንን አይጎዳውም፡፡

ልባችን በክፋት ከሚሰረቅ ይልቅ ወርቅና ብራችን ቢሰረቅ ይሻላል፡፡ የወርቅ እና የብር መሰረቅ እንደልባችን በክፉ ሃሳብ መበላሸት አይጎዳንም፡፡

አጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፥ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና። መጽሐፈ ምሳሌ 4:23

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa


 

No comments:

Post a Comment