Popular Posts

Thursday, April 11, 2019

ምርጫችንን እንጂ ህይወታችንን አንወስንም



ዛሬ የምንኖረው ኑሮ የትላንት ምርጫችን ውጤት ነው፡፡ ነገ የምንኖረው ኑሮ ደግሞ የዛሬ ምርጫችን ውጤት ነው፡፡ የትላንት ምርጫችንን እንጂ የዛሬ ኑሯችንን መወሰን እንደማንችል ሁሉ የዛሬ ምርጫችንን እንጂ የነገ ኑሯችንን መወሰን አንችልም፡፡
ዛሬ የምንወስነው ሃላፊነት የጎደለው ውሳኔ ነገ የሚያመጣውን መራራ ፍሬ እንድንጋፈጠው ያስገድደናል፡፡ ዛሬ የስንፍና ውሳኔ ወስኖ ነገ የስኬትን ውጤትን ለማግኘት መመኘት ትርፉ ድካም ነው፡፡ ዛሬ የፍርሃትን ውሳኔ ወስኖ ነገ የእምነትን ስኬት መጠበቅ ሞኝነት ነው፡፡ ዛሬ እግዚአብሄርን ባለመፈለግ በግብታዊነት ውሳኔ ወስኖ ነገ ህይወቴ ይከናወናል ብሎ መጠበቅ ከንቱ ነው፡፡
ከእሾህ ወይን ከኩርንችትስ በለስ ይለቀማልን? እንዲሁ መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬ ያደርጋል፥ ክፉም ዛፍ ክፉ ፍሬ ያደርጋል። መልካም ዛፍ ክፉ ፍሬ ማፍራት፥ ወይም ክፉ ዛፍ መልካም ፍሬ ማፍራት አይቻለውም። የማቴዎስ ወንጌል 7፡16-18
ዛሬ በስጋዊ ፍላጎት ወስኖ ነገ መንፈሳዊ ነገርን ማጨድ ዘበት ነው፡፡ ዛሬ ላይ በስጋዊ ሚዛን ውሳኔን ወስኖ ነገ በመንፈሳዊ ሚዛን ውጤቱን ለመቀበል መሞከር እግዚአብሄርን ለማታለል እንደመሞከር ነው፡፡  
አትሳቱ፤ እግዚአብሔር አይዘበትበትም። ሰው የሚዘራውን ሁሉ ያንኑ ደግሞ ያጭዳልና፤ በገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና፥ በመንፈስ ግን የሚዘራው ከመንፈስ የዘላለምን ሕይወት ያጭዳል። ወደ ገላትያ ሰዎች 6፡7-8
ስለትላንቱ ውሳኔያችን ንስሃ ገብቶ ከመመለስ ውጭ ምንም ላናደርግ እንችላለን፡፡ ነገር ግን ስለነገ ኑሯችን ዛሬ መልካምን ብቻ ለመዝራት መወሰን እንችላን፡፡
ሕይወትን ሊወድ መልካሞችንም ቀኖች ሊያይ የሚፈልግ ሰው፥ መላሱን ከክፉ ከንፈሮቹንም ተንኰልን ከመናገር ይከልክል፤ ከክፉ ፈቀቅ ይበል፥ መልካምንም ያድርግ፥ ሰላምን ይሻ ይከተለውም፤ የጌታ ዓይኖች ወደ ጻድቃን ናቸውና፥ ጆሮዎቹም ለጸሎታቸው ተከፍተዋል፥ የጌታ ፊት ግን ክፉ ነገርን በሚያደርጉ ላይ ነው። 1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 3፡10-12
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
#ክብር #ራእይ #ስጋ #ሃሳብ #የዘራውን #ያጭዳል #አትሳቱ #አይዘበትበትም #መበስበስ #ሰላም #ህይወት #ኢየሱስ #ክርስቶስ #ጌታ #ነገ #ዛሬ #ውሳኔ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #ብርሃን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #መንገድ #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

No comments:

Post a Comment