Popular Posts

Tuesday, October 4, 2016

ሞት - ድንገትኛ እንግዳ

ሞት ከስጋ መለየት ነው፡፡ ሰው በምድር ላይ ከሚኖርበት ምድራዊ መኖሪያ ስጋው ተለይቶ የሚወጣበት መንገድ ነው፡፡ ሞት መለየት ስለሆነና አንዳንዴም በድንገት ስለሚመጣና ህያውንና የተውን በድንገርት ስለሚለይ ሞትን በቀላሉ አንመለከተውም፡፡
ነገር ግን ወደድንም ጠላንም ግን ሞት አለ፡፡ ሞት ይጠብቀናል፡፡ ድንገተኛም ሞት ይሁን የተዘጋጀንበት ሞት ሁላችንንም ይጠብቀናል፡፡
ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደ ተመደበባቸው፥ ዕብራውያን 9፡27
ሰው በእግዚአብሄር አምሳል የተፈጠረ ዘላለማዊ ፍጥረት ነው፡፡ ሰው ከስጋም ከተለየም በኋላ መኖሩን አያቆምም፡፡ ሰው ከስጋ ከተለየም በኋላ ነፍሱና መንፈሱ ለዘላለም ይኖራል፡፡ ስለዚህ ነው ሞት መጥፊያ ማለቂያ መትነኛ ሳትይሆን ሞት ከተፈጥሮአዊው ወደመንፈሳዊው አለም መሸጋገሪያ ነው የሚባለው፡፡
ድሀውም ሞተ፥ መላእክትም ወደ አብርሃም እቅፍ ወሰዱት፤ ባለ ጠጋው ደግሞ ሞተና ተቀበረ። ሉቃስ 16፡22
ዋናው ነገር ግን ለሞት ተዘጋጅተናል ወይ የሚለውን ጥያቄ በሚገባ መመለስ ነው፡፡ ደግሞ ለሞት መዘጋጀት ምን አመጣው ትሉኝ ይሆናል፡፡ ወይም ደግሞ ሁላችንም መልካም ስራ ለመስራት እየሞከርን ነው ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡
ለሞት መዘጋጀት ማለት እግዚአብሄርን ለመገናኘት መዘጋጀት ማለት ነው፡፡ ሰው እግዚአብሄር ያዘጋጀለትን የመዳኛ መንገድ ኢየሱስን ከተቀበለ እግዚአብሄር ይቀበለዋል እግዚአብሄርን ለመገናኘት ተዘጋጅቷል፡፡
ሰው በእግዚአብሄር ተቀባይነት ለማግኘት በህይወቱ ሙሉ መስራትና መልፋት የለበትም፡፡ ገና ድሮ በሃጢያት ስለወደቅን እግዚአብሄርን ልናስደስትበት የምንችለው ምንም መልካም ምግባር የለም፡፡
አንድ ማድረግ የምንችለው ነገር ኢየሱስ ለሃጢያታችን የከፈለውን ሞት ለእኔ ነው ብለን በእምነት መቀበል ብቻ ነው፡፡
ሰው የሚዘጋጀው እግዚአብሄርን ለመገናኘት ነው፡፡ ሰው ከሃጢያት የሚድንበትን የመዳኛ መንገድ ከተቀበለ እግዚአብሄር ይቀበለዋል የዘላለምም ህይወት ይሰጠዋል፡፡ ይህ ሰው እግዚአብሄርን ለመገናኘት ተዘጋጅቶዋል እንላለን፡፡
ነገር ግን ሰውን ከእግዚአብሄር የለየውን የሃጢያቱን እዳ የከፈለውን እየሱስን ከጣለ እግዚአብሄር አይቀበለውም፡፡ ይህ ሰው ሳይዘጋጅ ሞተ እንላለን፡፡ መጨረሻውም ለዘላለም ከእግዚአብሄር መለየትና ጥፋት ነው፡፡
በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና። ዮሃነስ 3፡16
ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤ ዮሃንስ 1፡12
ሞት መቼ እንደሚመጣ ስለማናውቅ ማድረግ የምንችለው ብቸኛ ነገር እስትንፋሳችን እስካለ ድረስ ኢየሱስን መቀበልና ከእግዚአብሄር ጋር መታረቅ ነው፡፡ ያለን ቀን አሁን ነው፡፡
በተወደደ ሰዓት ሰማሁህ በመዳንም ቀን ረዳሁህ ይላልና፤ እነሆ፥ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤ እነሆ፥ የመዳን ቀን አሁን ነው። 2ኛ ቆሮንቶስ 6፡2
ጥያቄው ዛሬ ብትሞት እግዚአብሄርን ለመገናኘት ተዘጋጅተሃል ወይ ? እግዚአብሄር የሚጠይቅህ አንድ እርግጠኛ ጥያቄ ለሃጢያትህ ያዘጋጀሁትን ልጄን ኢየሱስን ተቀበልከው? ይሆናል፡፡
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
#ኢየሱስ #ጌታ #ራእይ #መዳን #እምነት #ሞት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #የዘላለምህይወት #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment