Popular Posts

Thursday, October 27, 2016

መንታ መንገድ

ከስር መሰረቱ መረዳት ከፈለግን የዘፍጥረት መፅሃፍ ስለሰው መጀመሪያ ብዙ ነገርሮችን ያስተምረናል፡፡ እግዚአብሄር ሰውን እንዴት እንደፈጠረውና የእግዚአብሄር የመጀመሪያው እቅዱ ምን እንደነበረ የምንረዳው በመጀመሪያ ያለውን ታሪክ ስናይ ነው፡፡ ሰውን እግዚአብሄር ሲፈጥረው ለክብሩ ነው የፈጠረው፡፡ ሰውን እግዚአብሄር ሲፈጥረው ሙሉ ለሙሉ በምድር ላይ እንዲወክለው ነው የፈጠረው፡፡ እግዚአብሄር ሰውን የፈጠረው በየዋህነት ሁሉ በፍፁም መታዘዝ እንዲከተለው ነው፡፡ በእርሱ ላይ ሙሉ መደገፍ አንዲኖረው ነው እግዚአብሄር ሰውን የፈጠረው፡፡
እግዚአብሔር አምላክም ሰውን እንዲህ ብሎ አዘዘው፦ ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና። ዘፍጥረት 2፡16-17
ሰው እግዚአብሄርን በሙሉ ቅንነት ሲከተል በነበረበት ጊዜ ሰው አንድነቱ ተጠብቆ በፍፁም ሰላም ይኖር ነበር፡፡ ሰው አንድ እውቀት ብቻ ነበር የነበረው፡፡ ሰው የነበረው እውቀት በእግዚአብሄር ላይ ሙሉ ለሙሉ በመደገፍ ከእግዚአብሄር ጋር መፍሰስ ነበር፡፡ ሰው በአንድ መንገድ ብቻ በህይወት ነበር የሚኖረው፡፡ ሰው እግዚአብሄርን መከተል ብቻ እንጂ መልካምንና ክፉን ማወቅና መለየት የለበትም ነበር፡፡ ሰው የህይወትን ዛፍ ፍሬ ብቻ ነበር የሚያውቀው በህይወትም ዛፍ ፍሬ ብቻ ነበር በህይወት የሚኖረው፡፡
ሰይጣን ወደ ሰው በቀረበ ጊዜ ግን ሁለትን እውቀት የምትሰጥን የዛፍ ፍሬ አስተዋወቀው፡፡ ሰው በህይወት ዛፍ ፍሬ በመኖርና መልካምና ክፉውን በምታሳውቀው ዛፍ ፍሬ መካከል መረጠ፡፡ ሰይጣን በአንድነት በህይወት ይኖር የነበረውን አዳምን ክፉና መልካም የምታስታውቀውን ሁለትን መንገድ አስተዋወቀው፡፡
ሰው ክፉውንም መልካምንም ቢመርጥ እንደ ህይወት ዛፍ ፍሬ መሆን አልቻለም፡፡ ሰው በእግዚአብሄር ላይ ያለውን ፍፁም መደገፍ ጣለ፡፡ አሁን ሰው በራሱ ማስተዋል መደገፍ አለበት፡፡ አሁን ሰው በራሱ "ይህ ክፉ ነው" "ይህ መልካም" ብሎ መለየት ነበረበት፡፡ ሰው በእግዚአብሔር ላይ በመደገፍ ብቻ ከእግዚአብሄር ጋር መፍሰስ አልቻለም፡፡
በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታመን፥ በራስህም ማስተዋል አትደገፍ፤ በመንገድህ ሁሉ እርሱን እወቅ፥ እርሱም ጎዳናህን ያቀናልሃል። በራስህ አስተያየት ጠቢብ አትሁን፤ ምሳሌ 3፡5-7
አሁንም በራሳችን ማስተዋል በመደገፍ የእግዚአብሄርን ፍፁም ሃሳብ መከተል አንችልም፡፡ የእግዚአብሄርን ሃሳብ በራሳችን ማስተዋል ልናገኘው በፍፁም አንችልም፡፡
ኢየሱስ ስለዚህ ነው ወደ ምድር የመጣውና የሃጢያት እዳችንን ሁሉ የከፈለው፡፡ ኢየሱስን የተቀበልን ሁላችን የእግዚአብሄር ልጆች ነን፡፡
አሁን የእግዚአብሄር መንፈስ በእኛ ውስጥ ይኖራል፡፡ አሁን ወደ ህይወት የሚመራው የህይወት መንፈስ ህግ በውስጣችን ይኖራል፡፡ በልባችን የሚኖረውን መንፈስን በቅንነት ከተከተልን እንደ እግዚአብሄር እንደልቡና እንደ ሃሳቡ ማድረግ እንችላለን፡፡ መንፈሱን በመከተል በህይወት መኖር እንችላለን፡፡
በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከኃጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና። ሮሜ 8፡2
መልካምና ክፉ ለመለየት በራሳችን ማስተዋል መደገፍ ትተን በውስጣችን የሚኖረውን መንፈስ ቅዱስን ብቻ በመከተል ከሃጢያትና ከሞት ህግ ነፃ መሆን እንችላለን፡፡
እናንተም ከቅዱሱ ቅባት ተቀብላችኋል፥ ሁሉንም ታውቃላችሁ። እናንተስ ከእርሱ የተቀበላችሁት ቅባት በእናንተ ይኖራል፥ ማንም ሊያስተምራችሁ አያስፈልጋችሁም፤ ነገር ግን የእርሱ ቅባት ስለ ሁሉ እንደሚያስተምራችሁ፥ እውነተኛም እንደ ሆነ ውሸትም እንዳልሆነ፥ እናንተንም እንዳስተማራችሁ፥ በእርሱ ኑሩ። 1ኛ ዮሐንስ 2፡20፣27
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
#ኢየሱስ #ጌታ #ምሪት #መንፈስ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ትጋት #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #የህይወትመንፈስህግ #መንፈስቅዱስ #በረከት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment