Popular Posts

Friday, June 10, 2016

የሚምሩ ብፁአን

በህይወታችን ስህተትን ልንሰራ እንችላል፡፡ በተሳሳትን ጊዜ ሁሉ በጣም የሚያስፈልገን ነገር ደግሞ ምህረት ነው፡፡ ምህረት ምን ያህል ጣፋጭ እንደሆነ የምንረዳው ጥፋት ያጠፋን ጊዜ ነው፡፡  

ሰውን መማር ይቅር ማለት ነው፡፡ ሰውን መማር በሰው ላይ አለመያዝ ነው፡፡ ሰውን መማር በእርምጃችን  ጥፋትን ከግምት ውስጥ አማስገባት ነው፡፡ ሰውን መማር ሰውን አለማሰርና መልቀቅ ነው፡፡ ሰውን መማር በሰው መንገድ ላይ አለመቆም ለሰው ውድቀትና አለመከናወን አስተዋፅኦ አለማድረግ ነው፡፡ ሰውን መማር ሰው በመንገዱ እንዲሄድ መተው ነው፡፡ ሰውን መማር ክፋት ከማድረግ ሃይላችን መታቀብ ነው፡፡ ሰውን መማር በሃሳባችን በንግግራችንና በድርጊታችን ለሌላው ውድቀት አለመስራት ነው፡፡

በህይወቴ ብዙ ጊዜ ሰዎች ምረውኝ ያውቃሉ፡፡ መማር እጅግ የሚያስደስት ነገር መሆኑን ዳግመኛ የምናስታውሰው በሰዎች እጅ ስንወድቅና ምህረታቸውን እጅግ ስንፈልግ ነው፡፡

የመማርን መልካምነት የተረዳ ሰው ሌላውን ሰው ለመማር ሁሌ ዝግጁ መሆን አለበት፡፡ እውነት ነው እንደ ንግግር ቀላል አይደለም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ከምችለው በላይ እንድንፈተን ስለማይፈቅድ ይቻላል፡፡ 1ኛ ቆሮንጦስ 10፡13

ሰው ምህረትን ሲያደርግላችሁ ደስ ይላል፡፡ ነገር ግን እናንተ ሰውን ስትምሩ ይበልጥ እጅግ ክብር ያለው ነገር ነው፡፡
እንዲያውም የሚምሩ ብፁአን ናቸው፤ ይማራሉና። ይላል እየሱስ ሲያስተምር፡፡ ማቴዎስ 5፡7

ሁሌ ካለማቋረጥ ብዙ ምህረትን የሚፈልግ ሰው በብዙ መማር ይጠበቅበታል፡፡  

ለሰው ምህረትን ማድረግ እኔም ልሳሳት እችላለሁ ምህረት የሚያስፈልገኝ ሰው ነኝ ብሎ ራስን በትህትና ማየትን ይጠይቃል፡፡ እርሱ ግን የሚሳሳት የማይመስለውና ሁሉን የሚያውቅ የሚመስለው ሰው ሌላውን መማር እንዳለበት አይታየውም፡፡

ለሰው ምህረትን የሚያደርግ ሰው ግን ይባረካል ብቻ ሳይሆን የተባረከ ሰው ነው፡፡ የሚምር ሰው ደስተኛ ፡ የተቀደሰና የሚደነቅ ሰው ነው፡፡ የሚምር የእግዚአብሄር ሰው ነው፡፡  የሚምር ሰው ሞገስ ያለው እድለኛ ሰው ነው፡፡

የሚምሩ ብፁአን ናቸው፤ ይማራሉና።

https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes

No comments:

Post a Comment