Popular Posts

Tuesday, June 14, 2016

የሚመለስ ፀሎት

መፀለይ እጅግ መታደል ነው፡፡ ይህን ታላቅ እድል በአግባቡ መጠቀም በህይወታችን ፍሬያማ እንድንሆን ያደርጋል፡፡
ፀሎት ሲባል አብዛኞቻችን ወደ ሃሳባችን የሚመጣው ለእግዚአብሄር መናገር ነው፡፡ ይህ አመለካከታችን እግዚአብሄር በፀሎት ውስጥ ያስቀመጠውን ሙሉ በረከት ተጠቃሚ እንዳንሆን ያደርጋል፡፡
ፀሎት መናገርን ይጨምራል እንጂ ፀሎት መናገር ብቻ አይደለም፡፡ ፀሎት እግዚአብሄርን መስማትና ለእግዚአብሄር መናገር ነው፡፡ ልብ አድርጉ ፀሎት ለእግዚአብሄር መናገርና እግዚአብሄርን መስማት ነው አላልኩም፡፡ፀሎት ከእግዚአብሄር መስማትና ለእግዚአብሄር መናገር ነው፡፡
በፀሎት እግዚአብሄርን መስማት ይቀድማል፡፡
እግዚአብሔር በሰማይ፥ አንተም በምድር ነህና በአፍህ አትፍጠን፥ በእግዚአብሔርም ፊት ቃልን ይናገር ዘንድ ልብህ አይቸኵል፤ ስለዚህም ቃልህ ጥቂት ትሁን። መክብብ 5፡2
አንደኛ ወደ እግዚአብሄ ስትመጣ ለመስማት ተዘጋጅተህ ና እንጂ ለመናገር አትቸኩል፡፡
ወደ እግዚአብሔር ቤት በገባህ ጊዜ እግርህን ጠብቅ፤ ለመስማት መቅረብ ከሰነፎች መሥዋዕት ይበልጣልና፤ መክብብ 5፡1
በፀሎት መስማት ቀዳሚ መሆኑን ብቻ ሳይሆን የፀሎት ዋናው ክፍል መስማት መሆኑን ማወቅ አለብን፡፡ ምክኒያቱም እንዴት እንድንፀልይ እንደሚገባን አናውቅምና ነው፡፡
እንዲሁም ደግሞ መንፈስ ድካማችንን ያግዛል፤ እንዴት እንድንፀልይ እንደሚገባን አናውቅምና፥ ነገር ግን መንፈስ ራሱ በማይነገር መቃተት ይማልድልናል፤ ሮሜ 8፡26
ፀሎት በአቦ ሰጥ የሚሆን ነገር አይደለም፡፡ እንደው የራሳችንን የግል ሃሳብ እንደመጣልን አነብንበን ሄደን ከእግዚአብሄር መልስ መጠበቅ አንችልም፡፡
ፀሎታችን እንዲመለስ ከፈለግን መንፈስ ቅዱስ ያለማወቅ ድካማችንን እንዲያግዝ ለመንፈስ ቅዱስ ጊዜ መስጠትና መንፈሱን እንዲያመለክተን መጠበቅ አለብን፡፡ መንፈሱን በልባችን መፈለግ መጠበቅና መስማት አለብን፡፡
የፀሎት ቀዳሚውና ዋናው ክፍል መንፈሱን መስማት ነው፡፡
አንዴ መንፈሱ ለጊዜው ለእኛ ያለውን ፈቃድ ካወቅን ብቻ ነው ያንን ለእግዚአብሄር መናገር የሚገባን፡፡ ስለዚህ ነው የፀሎት ዋናው ክፍል መስማት ነው የሚባለው፡፡
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakum/notes

No comments:

Post a Comment