Popular Posts

Friday, June 28, 2019

ወንድሙንም ደንቆሮ የሚለውም ሁሉ የገሃነመ እሳት ፍርድ ይገባዋል



እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፤ ወንድሙንም ጨርቃም የሚለው ሁሉ የሸንጎ ፍርድ ይገባዋል፤ ደንቆሮ የሚለውም ሁሉ የገሃነመ እሳት ፍርድ ይገባዋል። የማቴዎስ ወንጌል 5፡22
እግዚአብሄር አንድ ላይ እንድንኖር ማህበራዊ ፍጥረቶች አድርጎ ፈጥሮናል፡፡ እግዚአብሄር በህይወታችን ያለው ፍላጎት የሚያሟላው አጠገባችን ባለው ሰው ስጦታ ተጠቅሞ ነው፡፡ በምድር ላይ ያለነው በስጦታችን የሌላውን ሰው ፍላጎት ለማሟላት ነው፡፡
እግዚአብሄር ሲፈጥረን የተለያን አድርጎ ፈጥሮናል፡፡ ሁላችንም የተለያየ አስተሳሰብ ፣ አመለካከት ፣ ስጦታ ፣ ዝንባሌና  ፍላጎት ያለን ሰዎች ነን፡፡  ስላለን ትክክል ነው ብለን ስለምናምነው አስተሳሰብ ፣ አመለካከት ፣ ስጦታ ፣ ዝንባሌና  ፍላጎት ንስሃ እንደማንገባ ሁሉ ሌላውም ሰው ማንንም ይቅርታ ባይጠይቅ መገረም የለብንም፡፡ እኔ እስከ ልዩነቴ ሰዎች እንዲቀበሉኝ ወይም እንዲታገሱኝ እንደምፈልገው ሁሉ ሌላውም ሰው እንድንታገሰው ይፈልጋል፡፡
ሰዎችም ሊያደርጉላችሁ እንደምትወዱ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉላቸው። የሉቃስ ወንጌል 6፡31
በምድር ላይ ስኬታማ ለመሆን ልዩነታችንን መገንዘብ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ እንዲያውም በምድር ላይ ፍሬያማ ለመሆን ልዩነታችንን ተረድቶ እንደ ልዩነታችን መኖር ግዴታ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንኳን ያላደረገውን ሁሉንም ሰው አንድ አይነት ለማድረግ በሞከር ህይወትን ከማባከን የሰውን ልዩነት ለመቀበል ልብን ማስፋት ጥቅም አለው፡፡ የሰዎችን ልዩነት የማይረዳ ሰው በህይወቱ ስኬትንና ፍሬያማነትን ሳያይ ያልፋል፡፡
ከእኛ የተለዩ ብዙ ሰዎች ባሉበት ምድር ውስጥ መኖር ትህትናን ይጠይቃል፡፡ በፍፁም የማንረዳቸው ሰዎች ባሉበት ምድር ውስጥ ለመኖር ራስን ማዋረድ ይጠይቃል፡፡ በፍፁም የማይረዱን ሰዎች ባሉበት ምድር ውስጥ በሰላም መኖር መረዳትን ይጠይቃል፡፡ በፍጩም የማንረዳቸው ሰዎች ባሉነት መድር ወስጥ መኖር ራሰን መግዛት ይጠይቃል፡፡
ማናችንም ራሳችንን አልፈጠረንም፡፡ ሁላችንም እግዚአብሄር ለራሱ የፈጠረን የእግዚአብሄር ባሪያዎች ነን፡፡ የፈጠራቸው እግዚአብሄር አለ እንጂ ማናችንም ሌላውን ሰው አልፈጠርንም፡፡ ሰውም በመጨረሻ ተጠሪነቱ ለፈጠረው ለእግዚአብሄር እንጂ ለእርስ በእርሳችን አይደለም፡፡  
እኛ የእግዚአብሄር ፍጥረት እንደሆንን ሁሉ ወደድንም ጠላንም የማይመቸን ሰው የእግዚአብሄር ፍጥረት ነው፡፡ እኛን እግዚአብሄር እንደሚወደን ሁሉ ወደድንም ጠላንም በፍጹም የማይረዳንን ሰው ወዶታል፡፡ የእኛ ድርሻ እግዚአብሄር ከፈጠራቸው ሰዎች ጋር በትህትና መኖር ነው፡፡ ከእግዚአብሄር ጋረ በትህትና መሄዳችን የሚታየው ከፈጠራቸው ጋር በትህትና በመኖር ነው፡፡  
ሰው ሆይ፥ መልካሙን ነግሮሃል፤ እግዚአብሔርም ከአንተ ዘንድ የሚሻው ምንድር ነው? ፍርድን ታደርግ ዘንድ፥ ምሕረትንም ትወድድ ዘንድ፥ ከአምላክህም ጋር በትሕትና ትሄድ ዘንድ አይደለምን? ትንቢተ ሚክያስ 6፡8
ሌላውን መጣል የራስን አንድ የሰውነት ክፍል እንደመጣል ይቆጠራል፡፡ ሌላውን መጣል አንዱን በረከታችንን እንደመጣል ይቆጠራል፡፡ ሌላው ላይ መፍረድ ትእቢት ነው፡፡ ሌላው ላይ መፍረድ የእግዚአብሄርን ቦታ መውሰድ ነው፡፡ ሌላው ላይ መፍረድ ከእግዚአብሄር በላይ አውቃለሁ ማለት ነው፡፡ ሌላው ላይ መፍረድ አለም የምትተዳረው እንደ እግዚአብሄር ሳይሆን እንደ እኔ ህግ ነው ማለት ነው፡፡ ሌላው ላይ መፍረድ ማለት አለም ሰው መተዳደር ያለበት እንደእኔ መረዳት እንጂ እንደ እግዚአብሄር መረዳት አይደለም ማለት ነው፡፡  
በመፅሃፍ ቅዱስ ሌላውን መጣል እንደሚያስፈርድ የሚያስተምረው ስለዚህ ነው፡፡  
እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፤ ወንድሙንም ጨርቃም የሚለው ሁሉ የሸንጎ ፍርድ ይገባዋል፤ ደንቆሮ የሚለውም ሁሉ የገሃነመ እሳት ፍርድ ይገባዋል። የማቴዎስ ወንጌል 5፡22
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ህይወት #የሚፈርድ #የሚያማ #ወንጌል #መውደድ #ፍቅር #ደንቆሮ #የሚቆጣ #ፍርድ #ጨርቃም #ትህትና #መታዘዝ #ማገልገል #መውደድ #እውነት #ትህትና #ትንሳኤ #ህይወት #ወንጌል #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ  #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

No comments:

Post a Comment