Popular Posts

Thursday, June 13, 2019

እንዳለ


ያለ እምነትም ደስ ማሰኘት አይቻልም፤ ወደ እግዚአብሔር የሚደርስ እግዚአብሔር እንዳለ ለሚፈልጉትም ዋጋ እንዲሰጥ ያምን ዘንድ ያስፈልገዋልና። ወደ ዕብራውያን 11፡6
እንደ እውነቱ ከሆነ በእግዚአብሄር የማያምኑ ብዙ ሰዎች በምድር ላይ አሉ፡፡ እርሱም ብቻ አይደለም፡፡ እግዚአብሄርን የማያምኑ ብዙ የሃይማኖት ተከታዮች በምድር ላይ ይኖራሉ፡፡ እውነት ነው እግዚአብሄር የለም ብለው የሚያምኑ እና በግልፅ የሚናገሩ ሰዎች ጥቂቶች ናቸው፡፡ ነገር ግን በልባቸው እግዚአብሄር የለም የሚሉ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡ 
እግዚአብሔርን እንዲያውቁ በግልጥ ይናገራሉ፥ ዳሩ ግን የሚያስጸይፉና የማይታዘዙ ለበጎ ሥራም ሁሉ የማይበቁ ስለ ሆኑ፥ በሥራቸው ይክዱታል። ወደ ቲቶ 1፡16
እግዚአብሄርን የሚያውቁ እንደሆነ በአፋቸው የሚናገሩ ነገር ግን በስራቸው የሚክዱት ብዙ ሰዎችን ማግኘት ይቻላል፡፡
መፅሃፍ ቅዱስ ሰነፍ በልቡ እግዚአብሔር የለም ይላል፡፡ አስተውሉ ሰነፍ በአፉ አይደለም እግዚአብሔር የለም የሚለው፡፡ የሰነፍ በልቡ እግዚአብሔር የለም አስተሳሰብ የሚገለፀው በድርጊቱ ብቻ ነው፡፡ 
ሰነፍ በልቡ፦ አምላክ የለም ይላል። በሥራቸው ረከሱ፥ ጐስቈሉ፤ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም። መዝሙረ ዳዊት 141
በአፉ እግዚአብሄር አለ ብሎ የሚናገር ወይም እግዚአብሄር የለም ብሎ በአፉ የማይናገር ነገር ግን በልቡ እግዚአብሔር የለም የሚል የሰነፍ ሰውን ምልክቶችን እንመልከት፡፡
1.      እግዚአብሄርን እንደፈራጅ አያየውም
ሰው የፈለገውን ክፉ ነገር አድርጎ ከእርሱ በላይ ፈራጅ እንደሌለ እንደሚሄድ ካሰበ እግዚአብሄር እንዳለ አያምንም፡፡
2.     እግዚአብሄርን አይፈራም
ሰው ጥበቡ የማይመረመር ሃያል አምላክ እንዳል ካላመነ በስተቀር እግዚአብሄርን እንዴት ሊፈራ ይችላል፡፡ እግዚአብሄር እንዳለ የማያምን ሰው እግዚአብሄርን ሳይሆን ሰውን ይፈራል፡፡ በፊቱ ሁሉ ነገሮች የተራቆተና የተገለጠ አምላክ እንዳለ የማያምን ሰው ነገሮቹን ሁሉ በሰው ፊት ያደርጋል፡፡ ሁሉንም የሚያይ አምላክ እንዳለ የማያምን ሰው ከሰው በመደበቁ እና ሰውን በመዋሸቱ ብቻ እንደተሳካለት ያስባል፡፡  
እኛን በሚቆጣጠር በእርሱ ዓይኖቹ ፊት ሁሉ ነገር የተራቆተና የተገለጠ ነው እንጂ፥ በእርሱ ፊት የተሰወረ ፍጥረት የለም። ወደ ዕብራውያን 4፡13
3.     ባለው ነገር ይመካል ይታመናል
እግዚአብሄር እንዳለ የሚያምን ሰው እግዚአብሄርን ከመታመን ውጭ ምንም ሊያደርግ አይችልም፡፡ ባለው ነገር የሚታመን ሰው እግዚአብሄር እንዳለ አያምንም፡፡ እግዚአብሄር እንዳለ ባለማመኑ የሚመካበትና የሚደገፍነበት ቁሳቁስ ዝና እና ጥበብን ይፈልጋል፡፡
እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ጠቢብ በጥበቡ አይመካ፥ ኃያልም በኃይሉ አይመካ፥ ባለ ጠጋም በብልጥግናው አይመካ፤ ነገር ግን የሚመካው፦ ምሕረትንና ፍርድን ጽድቅንም በምድር ላይ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን በማወቁና በማስተዋሉ በዚህ ይመካ፤ ደስ የሚያሰኙኝ እነዚህ ናቸውና፥ ይላል እግዚአብሔር፡፡ ትንቢተ ኤርምያስ 9፡23-24
4.     እግዚአብሄር የምድር ባለቤት እንደሆነ አይታመንም
ሰው እግዚአብሄር እንዳለ ካላመነ  በምድር ላይ ያለውን ነገር ሁሉ እግዚአብሄር እንደፈጠረ እና እርሱ ባለቤት እንደሆነ አይረዳም፡፡ ሰው ምድር አንድ ባለቤት እንዳለው ሰው አስተዳዳሪ እና ባላአደራ እንጂ የምንም ነገር ባለቤት እንዳልሆነ የሚረዳው እግዚአብሄር እንዳለ ሲያመን ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንዳለ የማያምን ሰው በጊዜያዊነት በታማኝነት ተጠቅሞ ከማለፍ ይልቅ የምድር ነገር ባለቤት ለመሆን ሲፍጨረጨር ህይወቱን በከንቱ ይፈጃል፡፡
ከሕዝቡ መኳንንት ጋር ያስቀምጣቸው ዘንድ፥ የክብርንም ዙፋን ያወርሳቸው ዘንድ፥ ችግረኛውን ከመሬት ያስነሣል፥ ምስኪኑንም ከጉድፍ ያስነሣል፤ የምድር መሠረቶች የእግዚአብሔር ናቸውና፥ በእነርሱ ላይም ዓለምን አደረገ። መጽሐፈ ሳሙኤል ቀዳማዊ 2፡8
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#እምነት #ማየት #አለማየት #ቃል #የእግዚአብሄርሃይል #መንፈስቅዱስ #ቃሉንመስማት #እወጃ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

No comments:

Post a Comment