Popular Posts

Monday, March 27, 2017

የደቀመዝሙርነት 9 መስፈርቶች

በአለማችን ላይ እውነተኛ ደቀመዛሙርቶች አሉ፡፡ የስም ብቻ ደቀመዛሙርቶች ደግሞ አሉ፡፡ እውነተኛ ደቀመዝሙር የሚያደርገን ምን እንደሆነ ማወቅ በጣም ወሳኝ ነገር ነው፡፡ የእውነተኛ ደቀመዝሙርነት መንገድ ላይ መሆናችንን ማወቅ ህይወታችንን በከንቱ እንዳናባክነው ያደርገናል፡፡ እውነተኛ ደቀመዝሙርነታችን እውነተኛ ነፃነት ውስጥ ያስገባናል፡፡
ኢየሱስም ያመኑትን አይሁድ፦ እናንተ በቃሌ ብትኖሩ በእውነት ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ፤ እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው። ዮሐንስ 8፡31-32
የእውነተኛ ደቀመዝሙርነት መለያ 9 መፅሃፍ ቅዱሳዊ መስፈርቶች  
·         ጌታ ኢየሱስን ከሁሉም ነገር በላይ መውደድ

ኢየሱስን ከአባቱና ከእናቱን ከሚስቱም ከልጆቹም በላይ መውደድ አለበት፡፡ ከኢየሱስ በላይ የምንወደው ምንንም ነገር ካለ እውነተኛ ደቀመዛሙርት አልሆንም ማለት ነው፡፡

ማንም ወደ እኔ የሚመጣ ቢኖር አባቱንና እናቱን ሚስቱንም ልጆቹንም ወንድሞቹንም እኅቶቹንም የራሱን ሕይወት ስንኳ ሳይቀር ባይጠላ፥ ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም። ሉቃስ 14፡26

·         ራስን መካድ - ቃሉን ማስቀደም ትህትናና በእግዚአብሄር ፊት መዋረድ

እውነተኛ ደቀመዝሙርነት የሚለየው ራስን በመካድ ነው፡፡ ከእግዚአብሄርን ቃል ከነፍሳችን ፍላጎትና ጥቅም በላይ ማስቀደም ራስን መካድ ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቃል ለመጠበቅ ብለን ጥቅማችንን የምንተው ከሆነ ራሳችንን ክደናል፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል ለመታዘዝ ነፍሳችንን የምንክድ ከሆንን እውነተኛ የኢየሱስ ተከታዮች ነን፡፡   

ለሁሉም እንዲህ አላቸው፦ በኋላዬ ሊመጣ የሚወድ ቢኖር፥ ራሱን ይካድ መስቀሉንም ዕለት ዕለት ተሸክሞ ይከተለኝ። ሉቃስ 9፡23

·         ፍቅር - ከራስ ወዳድነት የፀዳ ህይወት

ደቀመዝሙር እግዚአብሄር የሚወደውን ሁሉ ይወዳል፡፡ እግዚአብሄር ሰዎችን ሁሉ እንደሚወድ ሁሉ የኢየሱስ ደቀመዝሙር ሰዎችህ ሁሉ ይወዳል፡፡ የሚጠላው ሰው ያለው ሰው እውነተኛ የኢየሱስ ደቀመዝሙር አይደለም፡፡

እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ፥ ደቀ መዛሙርቴ እንደ ሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ። ዮሐንስ 13፡35

·         በእግዚአብሄር መደገፍና መታመን

እውነተኛ ደቀመዝሙር ስለሁሉም ነገር በእግዚአብሄ ላይ መደገፍ አለበት፡፡ ባለው በምንም ነገር ላይ የሚደገፍ ሰው የኢየሱስ ደቀመዝሙር ሊሆን አይችልም፡፡ ደቀመዝሙር ስለሁሉም ነገሩ በእግዚአብሄር ላይ በመታመን እግዚአብሄርን ደስ የሚያሰኝ ነው፡፡  

እንግዲህ እንደዚሁ ማንም ከእናንተ ያለውን ሁሉ የማይተው ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም። ሉቃስ 14፡33

·         በእግዚአብሄር ድምፅ እለት እለት መመራት

እውነተኛ ደቀመዝሙር የራሱን ነገር አድርጎ አንዳንዴ እግዚአብሄርን የሚፈልግ ሳይሆን ለህይወቱ እለት እለት የእግዚአብሄርን ምሪት የሚፈልግ ነው፡፡ ደቀመዝሙር ከእግዚአብሄር ጋር የአባትና የልጅ ግንኙነት ያለውና እግዚአብሄርን ለማስደሰት ራሱ የሰጠ ነው፡፡

በጎቼ ድምፄን ይሰማሉ እኔም አውቃቸዋለሁ ይከተሉኝማል፤ ዮሃንስ 10፡27

·         ከኑሮ ፍርሃት እስራት መውጣት  

በኑሮ ፍርሃት የሚወጣና የሚገባ ሰው እውነተኛ የኢየሱስ ደቀመዝሙር አይደለም፡፡ እውነተኛ የኢየሱስ ደቀመዝሙር የእግዚአብሄርን ፅድቅና መንግስት ይፈልጋል፡፡ ሌላውን ሁሉ እንደሚጨመርለት ያውቃል፡፡ ሰው ለጌታም ለገንዘብም መገዛት ስለማይችል ገንዘብ የሚገዛው ሰው እውነተኛ የኢየሱስ ደቀመዝሙትር ሊሆ አይችልም፡፡  

የዚህም ዓለም አሳብና የባለጠግነት ማታለል የሌላውም ነገር ምኞት ገብተው ቃሉን ያንቃሉ፥ የማያፈራም ይሆናል። ማርቆስ 4፡19

·         ብዙ ፍሬን ማፍራት

እውነተኛ ደቀመዝሙር የሆነ ሰው የእግዚአብሄን ቃል በመኖር ለእግዚአብሄር ቤተክርስትያን በሁሉ ጠቃሚ ሲሆን ይታያል፡፡ ደቀመዝሙር ከክርስትያን እህቶችና ወንድሞች ጋር በፍቅር ይኖራል፡፡   

ብዙ ፍሬ ብታፈሩና ደቀ መዛሙርቴ ብትሆኑ በዚህ አባቴ ይከበራል። ዮሐንስ 15፡8

·         ክርስቶስን ይመስላል

እውነተኛ ደቀመዝሙር ትህትናው ፣ ትግስቱ ፣ የዋህነቱ ባህሪው ሁሉ ስለ እርሱ ይመሰክራል፡፡

የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፥ የውሃት፥ ራስን መግዛት ነው። ገላትያ 5፡22
·         ደቀመዝሙር ያፈራል

እውነተኛ ደቀመዝሙር በንፁህ የህይወት ምስክርነቱና የወንጌል ስብከት አገልግሎቱ ሌሎችን ደቀመዛሙርት ያፈራል፡፡

እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ። ማቴዎስ 28፡19-20

ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ

ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes

ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#እግዚአብሄር #ጌታ #መከተል #ቃል #ተማሪ #መንፈስቅዱስ #ቃሉንመስማት #ደቀመዝሙር #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #ነፍስንመካድ #መፅሃፍቅዱስ #ተከታይ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment