Popular Posts

Thursday, December 12, 2019

ለምን ግን ?



በእግዚአብሄር ፈቃድ ውስጥ ለመገኘትና በምድር ላይ የእግዚአብሄርን አላማ ለማስፈፀም ምን እያደረኩኝ ነው የሚለው ጥያቄ ብቻ ሳይሆን የማደርገውን ነገር የማደርገው ለምንድነው የሚለውን ጥያቄ መመለስ ወሳኝ ነው፡፡ የምናደርግው ነገር እስካልተቋረጠ ድረስ የምናደርግበትን ምክኒያት በትጋት መመርምር መቋረጥ የለበትም፡፡
ምን እያደረኩኝ ነው ከሚለው ጥያቄ ከመመለስ ያላነሰ የማደርገውን የማደርገው ለምንድነው የሚለውን ጥያቄ መለመለስ አስፈላጊ ነው፡፡  
እግዚአብሄር ምን እንድምታደርግ ብቻ ሳይሆን ለምን እንደምታደረገው ማወቅ ይፈልጋል፡፡ እግዚአብሄር ምን እንደምታደርግ ብቻ ሳይሆን ለምን እንድምታደርገው ግድ ይለዋል፡፡ 
የምታደርገው ትክክል ቢሆንም የምታደርግበት የልብህ መነሻ ሃሳብ ስህተት ሊሆን ይችላል፡፡ የምታደርገው ነገር መልካም ቢሆንም የልብህ ሃሳብ ክፉ ሊያደርገው ይችላል፡፡ የምታደርገው የተቀደሰ ቢሆንም የምታደርገበት ምክኒታት ሊያረክሰው ይችላል፡፡
መፀለይን የመሰለ የተቀደሰ ነገረ የለም፡፡ የምንፀልይበት የልባችን መነሻ ሃሳብ መፀለይን ሊያረክሰው ይችላል፡፡
ስትጸልዩም እንደ ግብዞች አትሁኑ፤ ለሰው ይታዩ ዘንድ በምኩራብና በመንገድ ማዕዘን ቆመው መጸለይን ይወዳሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። የማቴዎስ ወንጌል 6፡5
ምጽዋት ማድረግ የተባረከ ነገር ነው ነገር ግን ምጽዋት የምናደርግበት የልባችን መነሻ ሃሳብ የተረገመ ሊያደርገው ይችላል፡፡ 
እንግዲህ ምጽዋት ስታደርግ፥ ግብዞች በሰው ዘንድ ሊከበሩ በምኩራብ በመንገድም እንደሚያደርጉ በፊትህ መለከት አታስነፋ፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። የማቴዎስ ወንጌል 6፡2
የፀሎት እርዝማኔ ለሰው ካለን ርህራሄና ፍቅር ሳይሆን ከልባችን ስስትና ለጥቅም ያለ ስግብግብነት ሊመነጭ ይችላል፡፡
የመበለቶችን ቤት የሚበሉ ጸሎታቸውንም በማስረዘም የሚያመካኙ፥ እነዚህ የባሰ ፍርድ ይቀበላሉ አለ። የሉቃስ ወንጌል 20፡47
የምናደርገው ምንም መልካም ነገር በፍቅር ካልተደረገ ምንም አይጠቅመንም፡፡
በሰዎችና በመላእክት ልሳን ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮኽ ናስ ወይም እንደሚንሽዋሽዋ ጸናጽል ሆኜአለሁ። ትንቢትም ቢኖረኝ ምሥጢርንም ሁሉና እውቀትን ሁሉ ባውቅ፥ ተራሮችንም እስካፈልስ ድረስ እምነት ሁሉ ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ። ድሆችንም ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል፥ ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም። 1 ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 13፡1-3
ይህንን የማደርገው ለምንድነው ብለን በቅንነት ራሳችንን እንጠይቅ፡፡ ለራሳችን ግልፅ እንሁን፡፡ እውነተኛ መነሻ የልብ ሃሳባችንን እንጋፈጠው፡፡ ቢያንስ ለራሳችን ሃቀኛ እንሁን፡፡ ለራሳችን እውነተኞች እንሁን፡፡
በመጨረሻ ለዘመናት የገነባነው ህይወታችንና አገልግሎታችን በልብ የመነሻ ሃሳብ መበላሸት ከንቱ እንዳይሆን ልባችንን እንመርምር፡፡
ስለዚህም በጨለማ የተሰወረውን ደግሞ ወደ ብርሃን የሚያወጣ የልብንም ምክር የሚገልጥ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ጊዜው ሳይደርስ አንዳች አትፍረዱ፤ በዚያን ጊዜም ለእያንዳንዱ ምስጋናው ከእግዚአብሔር ዘንድ ይሆናል። 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 4፡5
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#እምነት #ሃሳብ #መነሻሃሳብ #ልብ #ንፁህ #ፍቅር #ፉክክር #ቃል #ክብር #የእግዚአብሔርቃል #ቃሉንመስማት #እወጃ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment