Popular Posts

Monday, November 25, 2019

ሥራ ፈቶች



እነዚህ ነገሮች ለእናንተ ሆነው ቢበዙ፥ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እውቀት ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንዳትሆኑ ያደርጉአችኋልና፤ እነዚህ ነገሮች የሌሉት ዕውር ነውና፥ በቅርብም ያለውን ብቻ ያያል፥ የቀደመውንም ኃጢአቱን መንጻት ረስቶአል። ስለዚህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ፤ እነዚህን ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉምና። 2ኛ የጴጥሮስ መልእክት 1፡8-10
ስንፈጠር ለስራ ለትጋት ለመከናወን ተፈጥረናል፡፡
በህይወት ደግሞ ገለልተኛ የሚባል ነገር የለም፡፡ ወይ አንዱን ይወዳል ሌላውን ይጠላል ወይ አንዱን ይንቃል ሌላውን ያከብራል፡፡
ለገንዘብ ያለመገዛት ፍቱን መድሃኒት ለእግዚአብሄር መገዛት ነው፡፡ ለእግዚአብሄር የሚገዛ ሰው ለገንዘብ መገዛት በህይወቱ ይሞታል፡፡ 
ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል፤ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም። የማቴዎስ ወንጌል 6፡24
ሰው ካልተጋ ስራ ፈት እና ፍሬ ቢስ ይሆናል፡፡ ሰው ከተጋ ፍሬያማ ደግሞ ይሆናል፡፡ በትጋትና በስራ ፈትነት መካከል ከሁለቱም ያለሆነ ምንም ገለልተኛ ስፍራ የለም፡፡
በአንድ ጊዜ ሁለት ነገር ማድረግ እንችልም፡፡ ራሳችንን ለአንድ ነገር ከሰጠን ለሌላው ተቃራኒ ነገር እንከለክላለን፡፡
የስጋን ነገር ካሰብን የመንፈስን ነገር ማሰብ አንችልም፡፡ የመንፈስን ነገር ካሰብን በቅፅበት የስጋን ነገር ከማሰብ ነጻ እንወጣለን፡፡
እንደ ሥጋ ፈቃድ የሚኖሩ የሥጋን ነገር ያስባሉና፥ እንደ መንፈስ ፈቃድ የሚኖሩ ግን የመንፈስን ነገር ያስባሉ። ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና፥ ስለ መንፈስ ማሰብ ግን ሕይወትና ሰላም ነው። ወደ ሮሜ ሰዎች 8፡5-6
ብልቶቻችንን የዓመፃ የጦር ዕቃ አድርገን ካቀረብን የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርገን ለእግዚአብሔር ማቅረብ አንችልም፡፡
ብልቶቻችሁንም የዓመፃ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ ለኃጢአት አታቅርቡ፥ ነገር ግን ከሙታን ተለይታችሁ በሕይወት እንደምትኖሩ ራሳችሁን ለእግዚአብሔር አቅርቡ፥ ብልቶቻችሁንም የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ ለእግዚአብሔር አቅርቡ። ወደ ሮሜ ሰዎች 6፡13
ራሳችንን ለጭንቀት ከሰጠን መፀለይና ጭንቀታችንን በጌታ ላይ መጣል አንችልም፡፡ ከፀለይን አቅማችንንና ጉልበታችንን ከጭንቀት መልሰን ወደ ፀሎት አናፈሰዋለን፡፡ ከፀለይን ጊዜያችንን ጉልበታችንን አቅማችንን በጭንቀት ላይ ከማዋል እንድናለን፡፡
የእግዚአብሄርን ቃል ለማመን ጊዜን ከሰጠን የእግዚአብሄርን ቃል ከሰማን እና ካሰላሰልን ቃሉን ማመን እንጂ መጠራጠር አንችልም፡፡
ኢየሱስም መልሶ፦ እውነት እላችኋለሁ፥ እምነት ቢኖራችሁ ባትጠራጠሩም፥ በበለሲቱ እንደ ሆነባት ብቻ አታደርጉም፤ ነገር ግን ይህን ተራራ እንኳ፦ ተነቅለህ ወደ ባሕር ተወርወር ብትሉት ይሆናል፤ የማቴዎስ ወንጌል 21፡21
ፍቅርን የምትከታተሉ ከሆነ ለጥላቻ ጊዜ ጉልበት አቅም አይተርፋችሁም፡፡
ፍቅርን ተከታተሉ፥ 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 14፡1
ሰይጣንን የመቃወሚያ ተዘዋዋሪ መንገድ ለእግዚአብሄር መገዛት ነው፡፡ ለእግዚአብሄር መገዛታችሁ በራሱ ዲያቢሎስን በህይወታችሁ እንድትቃወሙ ያደርጋችኋል፡፡ ለእግዚአብሄር መገዛታችሁ ዲያቢሎስ በህይወታችሁ ስፍራ እንዳይኖረው ያደርጋል፡፡
እንግዲህ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል፤ የያዕቆብ መልእክት 4፡7
በመንፈስ መመላለሳችሁ ከስጋ ስራ ጋር እንድትለያዩና የስጋን ስራ እንዳትፈፅሙ ያደርጋችኋል፡፡ ሰው የስጋን ምኞት ላለመፈፀም ከመንቀጥቀጥና ከመፍራት ይልቅ በመንፈስ ቢመላለስ ሳያውቀው የስጋን ስራ አይፈፅምም፡፡
ነገር ግን እላለሁ፥ በመንፈስ ተመላለሱ፥ የሥጋንም ምኞት ከቶ አትፈጽሙ። ወደ ገላትያ ሰዎች 5፡16
ሰው ማሰብ የሚችለው አንድ ነገር ብቻ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ቃል የሚያስብ ሰው ከእግዚአብሄር ቃል ውጭ ማሰብ ዜና ቦታ አይኖረውም፡፡
በቀረውስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ እውነተኛ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ጭምትነት ያለበትን ነገር ሁሉ፥ ጽድቅ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ንጹሕ የሆነውን ነገር ሁሉ፥ ፍቅር ያለበትን ነገር ሁሉ፥ መልካም ወሬ ያለበትን ነገር ሁሉ፥ በጎነት ቢሆን ምስጋናም ቢሆን፥ እነዚህን አስቡ፤ ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች 4፡8
ሰው የአለምን ነገር ላለማሰብ እና ላለማድረግ ከመፍጨርጨር ይልቅ የእግዚአብሄርን ነገር ለማሰብ ራሱን ቢሰጥ ከአለማዊነት ይድናል፡፡ 
የእግዚአብሔር ፈቃድ እርሱም በጎና ደስ የሚያሰኝ ፍጹምም የሆነው ነገር ምን እንደ ሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ። ወደ ሮሜ ሰዎች 12፡2
ሰው በተጠራበት ነገር ላይ ሲያተኩርና ሲተጋ ህይወቱ ከስራ ፈትነትና ከፍሬ ቢስነት ይድናል፡፡ ሰው የራሱ ስራ ከሌለው በሰው ስራ ውስጥ ራሱን ማግኘቱ እና ህይወቱን ማባከኑ አይቀሬ ነው፡፡ ሰው ስለተጠራበት ነገር ግልፅ ራእይ ከሌለው ጊዜውን እና ህይወቱን በሌላው ራእይ ላይ ያባክናል፡፡
ሥራ ከቶ ሳይሠሩ፥ በሰው ነገር እየገቡ፥ ያለ ሥርዓት ከእናንተ ዘንድ ስለሚሄዱ ስለ አንዳንዶች ሰምተናልና። 2ኛ ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች 3፡11
እነዚህ ነገሮች ለእናንተ ሆነው ቢበዙ፥ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እውቀት ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንዳትሆኑ ያደርጉአችኋልና፤ እነዚህ ነገሮች የሌሉት ዕውር ነውና፥ በቅርብም ያለውን ብቻ ያያል፥ የቀደመውንም ኃጢአቱን መንጻት ረስቶአል። ስለዚህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ፤ እነዚህን ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉምና። 2ኛ የጴጥሮስ መልእክት 1፡8-10
ሰው የህይወት መንፈስ ህግን ከተከተለ ከሃጢያትና ከሞት ህግ ነፃ ይወጣል፡፡ ሰው ሃጢያትን ላለመስራት ከመፍጨርጨር ይልቅ የህይወት መንፈስን ህግ መከተሉ በራሱ ከሃጢያት ያድነዋል፡፡
በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከኃጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና። ወደ ሮሜ ሰዎች 8፡2
ሰው ሌላውን ሰው ከባረከና ከፀለየለት እርሱን የሚጠላበት እና የሚረግምበት አቅም አይተርፈውም፡፡
ክፉን በክፉ ፈንታ ወይም ስድብን በስድብ ፈንታ አትመልሱ በዚህ ፈንታ ባርኩ እንጂ፥ በረከትን ልትወርሱ ለዚህ ተጠርታችኋልና። 1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 3፡9
ሰው ትኩረቱን የሰማያዊው ነገር ላይ ካደረገ በሚጠፋው የምድራዊ ነገር ላይ ማተኮር አይችልም፡፡
እንግዲህ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ፥ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ እሹ፤ በላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም። ወደ ቆላስይስ ሰዎች 3፡1-2
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#እምነት #ንስሃ #መመለስ #ሃጢያት #ይቅርታ #መንፈስቅዱስ #ቃሉንመስማት #መናዘዝ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

No comments:

Post a Comment