Popular Posts

Saturday, November 23, 2019

በእኛ እንደሚማልድ



ነገር ግን የሆነው ሁሉ፥ በክርስቶስ ከራሱ ጋር ካስታረቀን የማስታረቅም አገልግሎት ከሰጠን፥ ከእግዚአብሔር ነው፤ እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና፥ በደላቸውን አይቆጥርባቸውም ነበር፤ በእኛም የማስታረቅ ቃል አኖረ። እንግዲህ እግዚአብሔር በእኛ እንደሚማልድ ስለ ክርስቶስ መልክተኞች ነን፤ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናለን። 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 5፡18-20
በክርስቶስ ሞትና ትንሳኤ አምነትን የዳንን ሁላችን የክህንነት አገልግሎታችን ሁለት ነው፡፡ አንደኛው ስለሰው ለእግዚአብሄር መናገር ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ስለእግዚአብሄር ለሰው መናገር ነው፡፡
ስለሰው ለእግዚአብሄር የመናገር የክህንንት አገልግሎታችን የምልጃ አገልግሎታችን ነው፡፡ በጠላት ስለተያዙ ራሳቸውን ማዳን ስለማይችሉ ሰዎች ካሉበት እስራት ውስጥ ይወጡ ዘንድ ስለሰው በእግዚአብሄር ፊት እንቆማለን፡፡
ከእግዚአብሄር ጋር በክርስቶስ ኢየሱስ የታረቅን ሁላችን እግዚአብሄር የሰውን ክፋት እና አመፅ አይቶ እንዳይቀጣ እንዲራራ ይቅር እንዲል በእግዚአብሄርን በሰው መካከል እንቆማለን ስለሰዎች እንማልዳለን፡፡ ለራሳቸው መፀለይ ለማይችሉ ሰዎች በእነርሱ ቦታ ሆነን ህመማቸው ስቃያቸው እይተሰማን በእግዚአብሄር ፊት እንቆማለን እንለምናለን እንማልዳለን፡፡
እንግዲህ እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ሁሉ ጸጥና ዝግ ብለን እንድንኖር፥ ልመናና ጸሎት ምልጃም ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ። 1ኛ ወደ ጢሞቴዎስ 2፡1-2
ሁለተኛው የክህንነት አገልግሎታችን ስለእግዚአብሄር ለሰው መናገር ነው፡፡ ለእግዚአብሄር መንግስት አምባሳደሮች መልክተኞች ነን፡፡ እንደ ካህናት የእግዚአብሄርን ፍላጎትና ፈቃድ እናስፈፅማለን፡፡ እንደካህናት በህይወታችን የእግዚአብሄርን መንግስትና ፅድቅ ፍላጎት እናስቀድማለን፡፡ እንደ ካህናት ስለእግዚአብሄር መንግስት መስፋት አንሰራለን፡፡ እንደካህናት በህይወታችንም በንግግራችንም ስለእግዚአብሄር መንግስት በጎነት እንመሰክራለን፡፡
እንደካህናት ሰዎች የእግዚአብሄርን መልካምነት በህይወታችው አይተው እንዲማረኩ የእግዚአብሄርን በጎነት በህይወታችን በማንፀባረቅ በጎን በማድረግ እንተጋለን፡፡
መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ። የማቴዎስ ወንጌል 5፡16
እንደካህናት ሰዎች ከእግዚአብሄር ጋር እንዲታረቁ እንለምናለን፡፡ እንደካህናት የእግዚአብሄርን የፍቅር ልብ ለሰዎች እናሳያለን፡፡
እንግዲህ እግዚአብሔር በእኛ እንደሚማልድ ስለ ክርስቶስ መልክተኞች ነን፤ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናለን። 2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 5፡20
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ልመናና #ጸሎት #ምልጃ #ህይወት #ፋሲካ #ትንሳኤ #ሞት #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ማለፍ #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ 

No comments:

Post a Comment