Popular Posts

Thursday, July 18, 2019

የእግዚአብሔርን ባለጠግነት የምንካፈልበት ስልት



እግዚአብሄር ባለጠጋ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሁሉ በእጁ ሁሉ በደጁ የሆነ የሚጎድለው የሌለ ባለጠጋ አምላክ ነው፡
እርሱ ባጠጋ ሆኖ ልጆቹ እንዲያጡና እንዲጎድላቸው የሚፈልግ አባት እንደሌለ ሁሉ እግዚአብሄር ልጆቹም ያጡትንና የጎደላቸውን ነገር ይው እንዲልምኑት ይፈልጋል፡፡ ልጆቹ ከእርሱ ባለጠግነት ሙሉ ለሙሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እንደሚፈልግ አባት ሁሉ እግዚአብሄርም በፀሎት ከእግዚአብሄር ባለጠግነት ተካፋይ እንዲሆኑ ይፈልጋል፡፡
ልጆቹ ከእርሱ ባለጠግነት እንዲካፈሉ የሚፈልግ ጌታ የሰው ልጆች እንዲፀልዩ በብዙ ቦታዎች ያበረታታል፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ እግዚአብሄርን ያየው አንዳች እንኳን የለም በእቅፉ ያለው አንድ ልጁ ተረከው እንደሚል ኢየሱስ የእግዚአብሄርን ልብ ሲተርከው ሰዎች መፀለይ እንዳለባቸው በብዙ ቦታዎች በምሳና ካለ ምሳሌ በተደጋጋሚ ሲያስተምር እንመለከታለን፡፡  
በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል። የዮሐንስ ወንጌል 15፡7
ሳይታክቱም ዘወትር ሊጸልዩ እንዲገባቸው የሚል ምሳሌን ነገራቸው፥ እግዚአብሔር እንኪያስ ቀንና ሌሊት ወደ እርሱ ለሚጮኹ ለሚታገሣቸውም ምርጦቹ አይፈርድላቸውምን? እላችኋለሁ፥ ፈጥኖ ይፈርድላቸዋል። ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር እምነትን ያገኝ ይሆንን? የሉቃስ ወንጌል 18፡1፣7-8
እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ ይሰጣችኋል። እስከ አሁን በስሜ ምንም አልለመናችሁም፤ ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ለምኑ ትቀበሉማላችሁ። የዮሐንስ ወንጌል 16፡23-24
ኢየሱስ ስለፀሎት ያስተማረበትን ስንመለከት እግዚአብሄር ለልጆቹ ያልውን ቅናት እንመለከታለን፡፡ ልጆቹ ምን የመሰለ አባት በሰማይ እያላቸው ባለመለመናቸው ብቻ ከእግዚአብሄር ባለጠግነት ተካፋዮች አለመሆናቸውን አይቶ ይቀናል፡፡ ኢየሱስ ስለፀሎት ያስተማረውን ስንመለከት ልጆቹ ቶሎ ስለፀሎት ተረድተው እንዲፀልዩና ከእግዚአብሄር ባለጠግነት ተካፋይ እንዲሆኑ የቀናላቸውን የእግዚአብሄርን ቅናት እናስተውላለን፡፡
እስከ አሁን በስሜ ምንም አልለመናችሁም፤ የዮሐንስ ወንጌል 16፡24
እንደ እውነቱ ከሆነ መፀለይና መቀበል የሚገባንን ያህል አልተቀበልንም፡፡ የእግዚአብሄር ግምጃ ቤት ሙሉ ነው፡፡  
ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል። የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና፥ የሚፈልገውም ያገኛል፥ መዝጊያንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል። የማቴዎስ ወንጌል 7፡7-8
ብዙ ክርስትያኖች እግዚአብሄር አባታቸው ባለጠጋ ሆኖ እነርሱ ግን በጉድለት የሚኖሩበት ምክኒያት ለመፀለይ በመጀመሪያ ራሳቸውን ስለሚያዩ ነው፡፡ እግዚአብሄር በቃሉ እንደ ደሞዛችሁ መጠል ለምኑ ፣ እንደ ገቢያቹ መጠን ለምኑ ፣ እንደ ባንክ ሂሳባችሁ መጠን ለምኑ ያለ ይመስላቸዋል፡፡
እግዚአብሄር ግን ያው ለምኑ ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚያበረታን ካለምንም ቅድመ ሁኔታ እንድንለምን ነው፡፡
ሲጀመር የሚለምን ሰው የሚለመነው ነገር ያለው ሰው አይደለም፡፡ የሚለምን ሰው የጎደለው የሌለው ሰው ነው፡፡ የሚለምን ሰው እንዲኖረው የሚፈልግ እንጂ ያለው ሰው አይደለም፡፡  
ያለመቀበላችን ምክኒያት አለመለመናችን ነው፡፡
ነገር ግን አትለምኑምና ለእናንተ አይሆንም፤ የያዕቆብ መልእክት 4፡2
ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፈትላችሁማል። የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና፥ የሚፈልገውም ያገኛል፥ መዝጊያንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል። የማቴዎስ ወንጌል 7፡7-8
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.dinsa.37/notes
#ኢየሱስ #ጌታ #እግዚአብሔር #ለምኑ #ፈልጉ #አንኳኩ #ይቀበላል #ያገኛል #ይከፈትለታል #ቃል #ብልፅግና #ሃብት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #የእግዚአብሄርቃል  #የእግዚአብሔርፈቃድ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment