Popular Posts

Sunday, November 13, 2016

ባለስልጣኖች ሆይ - ደመወዛችሁም ይብቃችሁ


ቀራጮችም ደግሞ ሊጠመቁ መጥተው፦ መምህር ሆይ፥ ምን እናድርግ? አሉት። ከታዘዘላችሁ አብልጣችሁ አትውሰዱ አላቸው። ጭፍሮችም ደግሞ፦ እኛ ደግሞ ምን እናድርግ? ብለው ይጠይቁት ነበር። እርሱም፦ በማንም ግፍ አትሥሩ ማንንም በሐሰት አትክሰሱ፥ ደመወዛችሁም ይብቃችሁ አላቸው። ሉቃስ 3፡12-14
ቀረጥ ሰብሳቢዎችም ሊጠመቁ ወደ እርሱ መጥተው፣ “መምህር ሆይ፤ እኛስ ምን እናድርግ?” አሉት። እርሱም፣ “ከታዘዛችሁት በላይ ቀረጥ አትሰብስቡ” አላቸው። ወታደሮች ደግሞ፣ “እኛስ ምን እናድርግ?” ብለው ጠየቁት። እርሱም፣ “የማንንም ገንዘብ በግፍ አትንጠቁ፤ ሰውንም በሐሰት አትክሰሱ፤ ደመወዛችሁ ይብቃችሁ” አላቸው። ሉቃስ 3፡12-14 (አዲሱ መደበኛ ትርጉም)
መጥምቁ ዮሃንስ ከኢየሱስ አስቀድሞ የመጣ የሰዎችን ልብ ለእግዚአብሄር ሊያዘጋጅ የተላከ ነቢይ ነበር፡፡ ይህ ታላቅ ነቢይ ከተናገራቸው ነገሮች በመነሳት እግዚአብሄር ለህዝብ እንደሚያዝንና እንደሚቆረቆር ከዚህ ክፍል ልናይ እንችላለን፡፡ ነቢዩ በስልጣን ላይ ያሉት ባለስልጣኖች እንዴት መኖርና ህዝቡን ማገልገል እንዳለባቸው ያስተምራል፡፡
እግዚአብሄር ስልጣንን የሰጠው ህዝብ እንዲገለገልና እንዲጠቀም ነው፡፡ የስልጣን አላማው የህዝብ ፍትህና ሰላም ነው፡፡ እግዚአብሄር ለሰው በሰው ላይ ስልጣንን የመስጠቱ አላማ ህዝብ በሰላም ሰርቶ እንዲያድግና እንዲለወጥ ነው፡፡ ባለስልጣኖች በሰው ላይ ስልጣን የተሰጣቸው አላማው ሰውን ለማንሳትና ለማሳደግ ነው፡፡ ሰውን በትጋትና በታማኝነት ለማገልገል ያልተዘጋጀ ሰው ስልጣን ይጎዳዋል እንጂ አይጠቅመውም፡፡ በስልጣኑ ህዝብን ከለማገልገል ሌላ አላማ ያለው ሰው በእሳት እየተጫወተ ነው፡፡  
ሰዎች በስልጣናቸው ተጠቅመው ራሳቸውን ቢያገለግሉ እግዚአብሄር ይጠይቃቸዋል፡፡ እግዚአብሄር ስልጣንን የሰጠው ፍትህ እንዲሰፍንበት ነው፡፡ ሰዎች ግን ስልጣናቸውን ተጠቅመው እንዲንከባከቡት የተሰጣቸው ህዝብ ላይ ግፍን ቢሰሩ ከእግዚአብሄር ጋር ይጣላሉ፡፡
ብዙ ጊዜ ባለስልጣን የሚያገለግለውን ህዝብ የሚያስጨንቀውና የሚበዘብዘው ደሞዜ አይበቃኝም በማለት ነው፡፡ ለዚህ የእግዚአብሄር መልስ ደሞዛችሁ ይብቃችሁ የሚል ነው፡፡ አይበቃኝም በምትሉት በደሞዛችሁ እባርካችሁዋለሁ ይላል እግዚአብሄር፡፡ የላባችሁ ፍሬ ደሞዛችሁ ይብቃችሁ፡፡ የሰው ላብ አይጠቅማችሁም ይጎዳችሁዋል እንጂ፡፡ የሰው ሃዘን መንገዳችሁን ያዛባል፡፡ ሰው ከልቡ አዝኖባችሁ ትወድቃላችሁ እንጂ አትነሱም፡፡ ሰው አልቅሶባችሁ አይከናወንላችሁም፡፡
የታመነ ሰው እጅግ ይባረካል፤ ባለጠጋ ለመሆን የሚቸኵል ግን ሳይቀጣ አይቀርም።ምሳሌ 28፡20
በደሞዛችሁ በራሳችሁ ድካም ያላገኛችሁት ገንዘብ የእናንተ አይደለም፡፡ በድካማችሁ ያላገኛችሁት ሃብት መሰረት የለውም፡፡ በላባችሁ ያላገኛችሁት ሃብት ይበተናል፡፡ በድካማችሁ ያላገኛችሁት ሃብት እግዚአብሄር እንዲጠብቅላችሁ ወደ እግዚአብሄር ለመፀለይ እንኳን ድፍረቱ አይኖራችሁም፡፡
በችኰላ የምትከማች ሀብት ትጐድላለች፤ ጥቂት በጥቂት የተከማቸች ግን ትበዛለች። ምሳሌ 13፡11
ያላግባብ የተገኘ ገንዘብ እየተመናመነ ያልቃል፤ ገንዘቡን ጥቂት በጥቂት የሚያከማች ግን ይጠራቀምለታል። ምሳሌ 13፡11 (አዲሱ መደበኛ ትርጉም)
የእናንተ ደሞዛችሁ ከፍቅርና ከሰላም ጋር ይበቃችሁዋል፡፡   
እግዚአብሔርን ከመፍራት ጋር ያለ ጥቂት ነገር ሁከት ካለበት ከብዙ መዝገብ ይሻላል። የጐመን ወጥ በፍቅር መብላት የሰባ ፍሪዳን ጥል ባለበት ዘንድ ከመብላት ይሻላል። ምሳሌ 15፡16-17
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes

#ኢየሱስ #ጌታ #ባለስልጣን #ፀሎት #ወታደር #ቀራጭ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #ወንጌል #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment