Popular Posts

Thursday, October 26, 2017

ልጅ ስለሆንክ ብቻ

እግዚአብሄር የሚንከባከበን ስለሰራንና ወይም ስላልሰራን አይደለም፡፡ እግዚአብሄር የሚንከባከበን ልጅ ስለሆንን ብቻ ነው፡፡ የትኛው ወላጅ ነው በቤቱ የተወለደ ልጁ ስራ ሲሰራ የሚመግበው ካልሰራ ደግሞ ምግብን የሚከለክለው? ልጅ መሰረታዊ ፍላጎቱ የሚሟላው ልጅ ስለሆነና በቤተሰቡ ውስጥ ስለተወለደ ብቻ ነው፡፡  
ታዲያ የምንሰራው ለምድነው?
የምንሰራው የልጅነት መብታችንን ከእግዚአብሄር ለመቀበል አይደለም፡፡ የምንሰራው እግዚአብሄር ልጄን ምን አበላዋለሁ ብሎ ስለተጨነቀ እግዚአብሄርን ለመርዳት አይደለም፡፡ የምንሰራው ስራና በእግዚአብሄር ዘንድ ያለን የልጅነት መብት  ምንም የሚያገናኛቸው ነገር የለም፡፡ እግዚአብሄር ወፎችን የሚመግበው መስሪያ ቤት ሄደው ስለሰሩ አይደለም፡፡ የእግዚአብሄ ፍጥረት ስለሆኑ ብቻ ነው፡፡
ወደ ሰማይ ወፎች ተመልከቱ፤ አይዘሩም አያጭዱምም በጎተራም አይከቱም፥ የሰማዩ አባታችሁም ይመግባቸዋል፤ እናንተ ከእነርሱ እጅግ አትበልጡምን? ማቴዎስ 6፡26
የምንሰራው የክህንነት ሃላፊነታችንን ለመወጣት ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር በክርስቶስ ከራሱ ጋር ካስታረቀን በኋላ እኛን ካህናት አድርጎናል፡፡ ስለእግዚአብሄር ለሰዎች እንመሰከራለን፡፡ በድርጊትም በቃልም ሰዎችን ከእግዚአብሄር ጋር ታረቁ ብለን እንለምናለን፡፡ የእግዚአብሄር የምስራች ወንጌል መልክተኞች ነን፡፡  
የምንሰራው ለክርስቶስ ምስክርነታችን ሃይል እንዲሰጠን ነው፡፡ ክርስትያን ሰነፍ እንዳልሆነ እንዲያውም ጠንካራ ሰራተኛ እንደሆነና በእግዚአብሄር ፀጋ ተጨማሪ ምእራፍ የሚሄድ እንደሆንን በማሳየት በውስጣችን ስከለሚሰራወ የእግዚአብሄር ፀጋ ምስክር ለመሆን ነው፡፡
እንዲሁ በመቄዶንያ ሁሉ ላሉት ወንድሞች ሁሉ ታደርጋላችሁና። ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ከፊት ይልቅ ልትበዙ፥ በጸጥታም ትኖሩ ዘንድ ልትቀኑ፥ የራሳችሁንም ጉዳይ ልትጠነቀቁ፥ እንዳዘዝናችሁም፥ በውጭ ባሉት ዘንድ በአገባብ እንድትመላለሱ፥ አንዳችም እንዳያስፈልጋችሁ በእጃችሁ ልትሠሩ እንለምናችኋለን። 1ኛ ተሰሎንቄ 4፡10-12
ማንም ሰው አንድ ምዕራፍ ትሄድ ዘንድ ቢያስገድድህ ሁለተኛውን ከእርሱ ጋር ሂድ። ማቴዎስ 5፡41
የምንሰራው በስራ ቦታችን ላሉት ሰዎች ብርሃን ለመሆን ነው፡፡ የምንንሰራው ከፍ ያለ የእግዚአብሄር ህይወት እንዳለ ለማሳየት ነው፡፡ የምንሰራው የእግዚአብሄር ቃል ሊፈፅሙት የሚቻልና የሚገባ ክቡር ቃል እንደሆነ በህይወታችን ምሳሌ ለመሆን ነው፡፡ የምንሰራው በአካባቢያችን ላሉ ሰዎች የእግዚአብሄር መንግስትን መረዳት ለማካፈል ነው፡፡
እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ። በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሰወር አይቻላትም። መብራትንም አብርተው ከዕንቅብ በታች አይደለም እንጂ በመቅረዙ ላይ ያኖሩታል በቤት ላሉት ሁሉም ያበራል። ማቴዎስ 5፡14-15
የምንሰራው በስራ ለምንገናኛቸው ሰዎች የምድር ጨው ለመሆን ነው፡፡
የምንሰራው በስራ ለሚገናኙን ሰዎች በህይወታችን የእግዚአብሄር መልካምነትን ጣእም ለማቅመስ ነው፡፡
ለእያንዳንዱ እንዴት እንድትመልሱ እንደሚገባችሁ ታውቁ ዘንድ ንግግራችሁ ሁልጊዜ፥ በጨው እንደ ተቀመመ፥ በጸጋ ይሁን። ቆላስይስ 4፡6
ስራም ስንሰራ የመጀመሪያው ስራችን ለሰዎች የእግዚአብሄር መልካምነት ምስክር መሆን ነው፡፡ እንደ ክርስትያን የመጀመሪያ ጥሪያችን በህይወታችን ስለክርስትና መመስከር እንደመሆኑ መጠን ቀጣሪያችን የምድር ጌታችን ሳይሆን ቀጣሪያችን ጌታ ክርስቶስ ነው፡፡
እንደ ክርስትያን የመጀመሪያ ጥሪያችን ክርስቶስን በመምሰል ለሌሎች መመስከር እንደመሆኑ መጠን ቀጣሪያችንም ከፋያችንንም ጌታ ክርስቶስ ነው፡፡
ለሰው ሳይሆን ለጌታ እንደምታደርጉ፥ የምታደርጉትን ሁሉ በትጋት አድርጉት፥ ከጌታ የርስትን ብድራት እንድትቀበሉ ታውቃላችሁና፤ የምታገለግሉት ጌታ ክርስቶስ ነውና። ቆላስይስ 4፡23-24
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #ጭንቀት #ልጅነት #ብርሃን #ጨው #ምስክርነት #ጌታክርስቶስ #ርስት #ብድራት #ስራ #የኑሮሃሳብ #የእለትእንጀራ #የባለጠግነትምቾት #አቅርቦት #መሰረታዊፍላጎት #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment