Popular Posts

Tuesday, October 31, 2017

40 የእምነት ጥቅሞች (ክፍል ሁለት) ዕብራውያን 11፡21-40

እግዚአብሄር መንፈስ ነው፡፡ እግዚአብሄር በስጋ አይን አይታይም፡፡ እግዚአብሄር ምን እንደሚሰራ ለማየትና ከእርሱ ጋር ለመስማማትና ለመተባበር የመንፈስ አይን ይጠይቃል፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር በሚገባ ለመኖር በተፈጥሮአዊ አይን የማይታየውን ማየት ይጠይቃል፡፡ ወደ እግዚአብሄር ለመድረስ እግዚአብሄርን ማመን ይጠይቃል፡፡ ወደ እግዚአብሄር ለመድረስ እምነት ይጠይቃል፡፡ እግዚአብሄርን ለመንካት እምነት ይጠይቃል፡፡ ከእግዚአብሄር ሃይል ጋር ለመገናኘት እምነት ይጠይቃል፡፡ የእግዚአብሄር አቅርቦት ተጠቃሚ ለመሆን እምነት ይጠይቃል፡፡
በአጠቃላይ ያለእምነት እግዚአብሄርን ማስደሰት አይቻልም፡፡ ያለእምነት ከእግዚአብሄር ጋር ያለው ግንኙነታችን ትክክል ሊሆን በፍፁም አይችልም፡፡ ካለእምነት ከእግዚአብሄር ጋር ልንገናኝ አንችልም፡፡  
እምነት በተፈጥሮአዊ አይናችን የማናየውን ተስፋ ለማረጋገጥ ይጠቅማል፡፡ እምነት በተፈጥሮ አይናችን ስለማናየው ነገር ያስረዳል፡፡
እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው። ዕብራውያን 11፡1
ሰው ስለተለያየ ነገር ሊመሰክር ይችላል፡፡ የእግዚአብሄር እውነተኛው ምስክርነት የሚገኘው ግን በእምነት ከመኖር ነው፡፡ እምነት የእግዚአብሄር ምስክርነት እንዲኖረን ያደርጋል፡፡
ለሽማግሌዎች የተመሰከረላቸው በዚህ ነውና። ዕብራውያን 11፡2
ስለማናየው ስለወደፊቱ የበረከትን ቃል የምንለቀው በእምነት ብቻ ነው፡፡ የበረከታችን ቃል እንደሚደርስ አውቀን የምናመሰግነው በእምነት ነው፡፡
ያዕቆብ ሲሞት በእምነት የዮሴፍን ልጆች እያንዳንዳቸው ባረካቸው፥ በዘንጉም ጫፍ ተጠግቶ ሰገደ። ዕብራውያን 11፡21
ስለወደፊት ህይወታችንና ስለትውልዳችን የምናየው እና የምንናገረው በእምነት ነው፡፡
ዮሴፍ ወደ ሞት ቀርቦ ሳለ በእምነት ስለ እስራኤል ልጆች መውጣት አስታወሰ፥ ስለ አጥንቱም አዘዛቸው። ዕብራውያን 11፡22
ካለፍርሃት የምድራዊውን ህግ ሽረን እግዚአብሄርን የምንታዘዘው በእምነት ነው፡፡
ሙሴ ከተወለደ በኋላ ወላጆቹ ያማረ ሕፃን መሆኑን አይተው በእምነት ሦስት ወር ሸሸጉት የንጉሥንም አዋጅ አልፈሩም። ዕብራውያን 11፡23
ስለ ጥሪያችን ስንል የምድራዊውን ጥቅም የምንንቀው በእምነት ነው፡፡ ራሳችንን ከምድራዊ ፉክክር የምናገለው በተፈጥሮ አይን የማይታየውን በማየት በእምነት ነው፡፡
ሙሴ ካደገ በኋላ የፈርዖን የልጅ ልጅ እንዳይባል በእምነት እምቢ አለ፤ ዕብራውያን 11፡24
እግዚአብሄር ክብደት ለሰጠው ነገር ክብደት የምንሰጠውና የናቀውን ነገር ደግሞ የምንንቀው በእምነት ነው፡፡ ከጊዜያዊ ደስታ ይልቅ የዘላለሙን ብድራት የምናየው በእምነት ብቻ ነው፡፡ በእግዚአብሄር ፈቃድ ውስጥ ያለ ማንኛውም ነገር የሚበልጥ ባለጠግነት እንደሆነ የምናስተውለው በእምነት ብቻ ነው፡፡ በምድር ላይ ትኩረታችን ለሚፈልጉ ነገሮችን እንቢ የምንለውና ክርስቶስን ብቻ ተመልክተን ሩጫችንን በትእግስት የምንጨርሰው በእምነት ነው፡፡
ከግብፅም ብዙ ገንዘብ ይልቅ ስለ ክርስቶስ መነቀፍ እጅግ የሚበልጥ ባለ ጠግነት እንዲሆን አስቦአልና ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ፤ ብድራቱን ትኵር ብሎ ተመልክቶአልና። ዕብራውያን 11፡25-26
በምድር ላይ የሚያስፈራሩትንና የሚያስጨንቁትን ነገሮች ሳንፈራ እግዚአብሄርን የምናገለግለው በእምነት ነው፡
የንጉሡን ቍጣ ሳይፈራ የግብፅን አገር የተወ በእምነት ነበር፤ የማይታየውን እንደሚያየው አድርጎ ጸንቶአልና። ዕብራውያን 11፡27
ለሩሮዋችን ሳንጨነቅ የእግዚአብሄርን መንግስትና ፅድቅ የምንፈልገው በእምነት ነው፡፡

ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል። ማቴዎስ 6፡33
በመውጣት በመግባታችን ከክፉ የምንጠበቀው በእምነት ነው፡፡ በአእምሮ የማይመስለውን የእግዚአብሄርን ቃል በሞኝነት የምንታዘዘው በእምነት ነው፡፡
አጥፊው የበኵሮችን ልጆች እንዳይነካ ፋሲካንና ደምን መርጨትን በእምነት አደረገ። ዕብራውያን 11፡28
ከከበበን ነገር የምናልፈው በእምነት ነው፡፡
በደረቅ ምድር እንደሚያልፉ በኤርትራ ባሕር በእምነት ተሻገሩ፥ የግብፅ ሰዎች ግን ሲሞክሩ ተዋጡ። ዕብራውያን 11፡29
ከእኛ ሃየለ የሚበልጠውን በሰው ጉልበት የማይቻለውን አስፈሪውን የጠላትን ግዛት የምንወርሰው በእምነት እርምጃ በመውሰድ ነው፡፡
የኢያሪኮ ቅጥር ሰባት ቀን ከዞሩበት በኋላ በእምነት ወደቀ። ዕብራውያን 11፡30
የእግዚአብሄር ፈቃድ የምንታዘዘው በተፈጥሮአዊ አይናችን አይተን ሳይሆን ቃሉን ብቻ ሰምተን በእምነት በመታዘዝ ነው፡፡
ጋለሞታይቱ ረዓብ ሰላዮችን በሰላም ስለ ተቀበለቻቸው ከማይታዘዙ ጋር በእምነት አልጠፋችም። ዕብራውያን 11፡31
በምናልፍበት አስቸጋሪ ህይወት ድልን የምናገኘው በእምነት ነው፡፡ የተሰጠንን የተስፋ ቃል የምናገኘው በእምነት ነው፡፡
እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥ ዕብራውያን 11፡33
ከሰው ሃይልና ችሎታ በላይ የሆኑ ታእምራት በህይወታችን የሚሆኑት በእምነት ነው፡፡ የእሳት ሃይል የማይጎዳን በችሎታችን ሳይሆን በእግዚአብሄ ችሎታ ላይ በመታመን ነው፡፡ ከድካም የምንበረታው በእምነት ነው፡፡ ከእኛ እጅግ የሚበረቱትን ድል የምንረታው በእምነት ነው፡፡  
የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ። ዕብራውያን 11፡34
ክርስትና ህይወታችንን መስዋእት እስከምናደርግ ድረስ ለጥሪያችን የምንታዘዘው በእምነት ነው፡፡
ሴቶች ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ ዕብራውያን 11፡35
ሰው የሚጋደልለትን ነገር በደስታ የምናጣው የተሻለ ነገር እንዳለ በእምነት አይናችን አይተን ነው፡፡
የሚበልጥና ለዘወትር የሚኖር ገንዘብ በሰማይ ራሳችሁ እንዳላችሁ አውቃችሁ፥ በእስራቴ ራራችሁልኝ የገንዘባችሁንም ንጥቂያ በደስታ ተቀበላችሁ። ዕብራውያን 10፡34
የሰዎች መሳለቂያ የምንሆነው በእምነት ነው፡፡ ክብራችንን የምንተወው በእምነት ነው፡፡ ሰው የሚያከብረውን እንዳይደርስበት ሁሉንም ነገር የሚያደርገለትን ነውር የምንንቀው በእምነት ነው፡፡
ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ ዕብራውያን 11፡36
የእግዚአብሄርን ስራ ለመስራት መዋረድን የማንፈራው በእምነት ነው፡፡ እግዚአብሄርን ለመታዘዝ መሳለቂያ መሆንን የምንንቀው በእምነት ነው፡፡  
. . . የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና። ዕብራውያን 12፡1-2
ማጣትን የምንንቀው በእምነት ነው፡፡ ላለማጣት ማንኛውንም ነገር የማናደርገው በእምነት ነው፡፡
በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ዕብራውያን 11፡37
ማጣት እንደማያዋርደን ማግኘት እንደማያከብረን የሚያኖረን እግዚአብሄር እንደሆነ የምንረዳው በእምነት ነው፡
መዋረድንም አውቃለሁ መብዛትንም አውቃለሁ፤ በእያንዳንዱ ነገር በነገርም ሁሉ መጥገብንና መራብንም መብዛትንና መጉደልን ተምሬአለሁ። ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ። ፊልጵስዩስ 4፡12-13
የአለምን ጥቅም የምንንቀው ፣ በአለም የማንጠቀመውና በአለም ጥቅም ላይ የሙጥኝ የማንለው በእምነት ነው፡፡
ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ። ዕብራውያን 11፡38
የሚገዙም ምንም እንደሌላቸው፥ በዚችም ዓለም የሚጠቀሙ በሙሉ እንደማይጠቀሙባት ይሁኑ፤ የዚች ዓለም መልክ አላፊ ነውና። 1ኛ ቆሮንቶስ 7፡31
በእምነታቸው የተመሰከረላቸው አባቶች ያመኑትን ነገር ሳያገኙ የሞቱት በእምነት ነው፡፡
እነዚህም ሁሉ በእምነታቸው ተመስክሮላቸው ሳሉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አላገኙም፥ ያለ እኛ ፍጹማን እንዳይሆኑ እግዚአብሔር ስለ እኛ አንዳች የሚበልጥ ነገርን አስቀድሞ አይቶ ነበርና። ዕብራውያን 11፡39-40
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #እምነት #መናገር #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #እምነት #ቃል #ማሰላሰል #ማድረግ #ሁሉይቻላል #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

No comments:

Post a Comment