Popular Posts

Saturday, August 13, 2022

የክርስትና ሚሊየነርነት

 

በአለም ላይ የተለያዩ የክንውን መመዘኛዎች አሉ፡፡ እያንዳንዱ የስኬት መመዘኛ እንደዋጋ አሰጣጡ ይለያያል፡፡

በክርስትናም "ይህ ሰው ኑሮው ሲያስቀና ውይ ታድሎ" የሚባልለት ሰው አለ፡፡ በክርስትና የተሳካለት የተከናወነለት የሚባለው ሰው ምን አይነት ሰው እንደሆነ የህይወት መመሪያችን የሆነው በህይወታችን ላይ የመጨረሻው ስልጣን ያለው መፅሃፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡  

በክርስትና "ይህ ሰው ሲያስቀና" የሚባልለት እና እጅግ የተከናወነለት ሰው እግዚአብሄርን ስለ መሰረታዊ ፍላጎቱ የሚያምን እና ጌታን የሚከተለ ሰው ነው፡፡

እንግዲህ፦ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን? ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤ ይህንስ ሁሉ አሕዛብ ይፈልጋሉ፤ ይህ ሁሉ እንዲያስፈልጋችሁ የሰማዩ አባታችሁ ያውቃልና። ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል። ማቴዎስ 6፡31-33

ለሰው ልጅ መሰረታዊ ፍላጎቱን አሟልቶ ጌታን ከመከተል በላይ የስኬት እና የክንውን ጣራ የለም፡፡ ሰው መሰረታዊ ፍላጎቱን አሟልቶ ጌታን ከተከተለ ከእርሱ በላይ በእውነት የተከናወነለት ሰው በምድር ላይ የለም፡፡

ኑሮዬ ይበቃኛል ለሚለው ግን እግዚአብሔርን መምሰል እጅግ ማትረፊያ ነው፤ ወደ ዓለም ምንም እንኳ አላመጣንምና፥ አንዳችንም ልንወስድ አይቻለንም፤ ምግብና ልብስ ከኖረን ግን፥ እርሱ ይበቃናል። 1ኛ ጢሞቴዎስ 6፡6-8

ከምትበላው ከምትጠጣው ከምትለብሰው በላይ እግዚአብሄር ቢሰጥህ ለአንተ አይደለም፡፡ አንተ የተሰጠህ ሃብት ባለ አደራ እንጂ ባለቤት አይደለህም፡፡ እግዚአብሄር ድርጅት ቢሰጥህ ብዙዎች ተቀጥረው ቤተሰባቸውን የሚያስተዳድሩበት የልጃቸውን የትምህርት ቤት የሚከፍሉበት እንጂ የአንተ አይደለም፡፡

ምንም ባለሃብት ብትሆን ከመሰረታዊ ፍላጎት ከምትበላው ፣ ከምትጠጣው እና ከምትለብሰው በላይ አትጠቀምም፡፡ ምንም ዝና ቢኖርህ ሰዎች እንዲቀበሉህ እና በውስጥ ያለውን ክህሎት እንዲጠቀሙ የተሰጠህ ስጦታ እንጂ የአንተ ሃብት አይደለም፡፡ ምንም ሃያል ብትሆን እንድትባርክበት የተሰጠህ እድል እንጂ የአንተ ሃብት አይደለም፡፡ ምንም ጥበበኛ ብትሆን ለሰዎች በህይወት የሚያሸንፉበትን ጥበብ እንድታካፍል የተሰጠህ ስጦታ እንጂ የአንተ አይደለም፡፡   

የእኔ ነው የምትለው እውነተኛው ሃብት እና የስኬት ጣሪያው ለመሰረታዊ ነገር ጌታን ማመን እና ጌታ ኢየሱስን ማመን እና መከተል ብቻ ነው፡፡ 

No comments:

Post a Comment