Popular Posts

Wednesday, November 7, 2018

የእስራኤል ዳንሳ ንግግር በእግዚአብሄር ቃል ሲፈተሽ

ነቢይ የእግዚአብሄር አፍ ነው፡፡ ነቢይ ከለአግዚአብሄር ሰምቶ የሚናገር ነው፡፡ ነቢይ የእግዚእብህር በልቡና ያለውን ተረድቶ ለህዝቡ የሚገልፅ ነው፡፡
በድሮ ዘመን ብቻ ሳይሆን እግዚአብሄር ነቢይን በዚህ በእኛ ዘመን እንደሚያስነሳ ከእግዚአብሄር ቃል እንረዳለን፡፡  
እውነተኛ ነቢያት ባሉበት ሁሉ ግን ሃሳተኛ ነቢያት ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ እውነተኛ ነቢያት በፊትም እንደነበሩ አሁንም እውነተኛ ነቢያት አሉ፡፡ ሃሰተኛ ነቢያት በፊትም እንደነበሩ አሁንም ሃሰተኛ ነቢያት አሉ፡፡ የሃሰተኛ ነቢያት መኖር የእውነተኛ ነቢያትን መኖር እንጂ አለመኖር አያሳይም፡፡
ማንኛውም ሰው እንደሚሳሳት ሁሉ ነቢይ ሊሳሳይት ይችላል፡፡ ነቢይ ሲሳሳት ግን እንደማንኛውም አገልጋይ ፈጥኖ ንስሃ መግባትና ከስህተቱ መመለስ አለበት፡፡ ነቢይ በአንድ ነገር ተሳሳተ ማለት ደግሞ በሁሉም ነገር ተሳሳተ ማለት አይደለም፡፡ እያንዳንዱ ቃሉና ድርጊቱ በእግዚአብሄር ቃል መመርመር ይኖርበታል፡፡
ከእግዚአብሄር ቃል በላይ የሆነ አገልጋይም አገልግሎትም የለም፡፡ የነቢይ ብቻ ሳይሆን የማንም ሰው አገልግሎት በእግዚአብሄር ቃል መፈተሽ አለበት፡፡
አንዳንድ የስህተት ነቢያት የሚያደርጉትናና የሚናገሩትን ስናይ ነቢያትን በደፈናው ላለመቀበል አንፈተናለን፡፡ መፅሃፍ ቅዱስ ትንቢትን አትናቁ ሲለን ከምናያቸውና ከምንሰማቸው አንዳንደ የተሳሳቱ ነገሮች አንፃር ትንቢትን በደፈናው እንዳንጥል እያስጠነቀቀን ነው፡፡ ነቢያት አንዳንድ ከእግዚአብሄር ቃል ውጭ የተናገሩት ነገር አለ ብለን የሚናገሩትን ሁሉ መጣል የለብንም፡፡ አንዳንድ የስህተት ነቢያት ስላሉ ብቻ እግዚአብሄር በትክክለኛው ነቢያት ውስጥ ያስቀመጠልንን ፀጋ እንዳንገፋ የእግዚአብሄር ቃል ያስጠነቅነቀናል፡፡  
መፅሃፍ ቅዱስ ደግሞ ትንቢትን መርምሩም ይለናል፡፡ ነቢይ ስለተናገረ ብቻ መቀበል ጥፋት ነው፡፡ የነቢይም ይሁን የማንኛውም አገልጋይ ንግግር ወይም ድርጊት በእግዚአብሄር ቃል መፈተን አለበት፡፡ ከእግዚአብሄር ቃል ጋር የማይሄድ ማንኛውም ንግግር ማንም ይናገረው ማን ተቀባይነት የለውም፡፡
መንፈስን አታጥፉ፤ ትንቢትን አትናቁ፤ ሁሉን ፈትኑ መልካሙንም ያዙ፤ 1ኛ ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች 5፡19-21
ከዚህ በፊት በፃፍኳቸው ፅሁፎች ነቢይነት ምን እንደሆነ እንዲሁም የነቢይትነት ፈተናዎች ምን አንደሆኑ ጠቃቅሻለሁ፡፡ አሁን ግን ይህን ፅሁፍ ለመፃፍ ያነሳሳኝ የእስራኤል ዳንሳ ንግግር ነው፡፡
የዚህ ፅሁፍ አላማ እስራኤል ዳንሳ ስህተተኛ ነቢይ ነው ወይስ ትክክለኛ ነቢይ ነው የሚለውን ጥያቄ መመለስ አይደለም፡፡  
የዚህ ፅሁፍ አላማ እስራኤል ዳንሳ የተናገረውን አንድ ንግግር በማንሳት እንደ እግዚአብሄር ቃል ትክክል ነው አይደለም የሚለውን መለየት ነው፡፡  
ነቢያትም ሁለት ወይም ሦስት ሆነው ይናገሩ ሌሎችም ይለዩአቸው፤ 1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 14፡29
በመጀመሪያ ደረጃ ነቢይነት ይሁን ሌሎች የአገልግሎት ስጦታዎች በሰው ፈቃድ የሚመጡ አይደሉም፡፡ ነቢይነት የእግዚአብሄር ስጦታ ነው፡፡ እግዚአብሄር እንደወደደ አንዳንዶቹን ብቻ ነቢያት በማድረግ ለቤተክርስትያን ሰጥቶዋል፡፡ ነቢይነት እግዚአብሄር እንደወደደ ለአንዳንዶች የሚሰጠው የአገልግሎት ስጦታ ነው፡፡
እርሱም አንዳንዶቹ ሐዋርያት፥ ሌሎቹም ነቢያት፥ ሌሎቹም ወንጌልን ሰባኪዎች፥ ሌሎቹም እረኞችና አስተማሪዎች እንዲሆኑ ሰጠ፤ ወደ ኤፌሶን ሰዎች 4፡11
ነቢይነት ወይም ሌላ ማንኛውም የአገልገሎት ስጦታ በሰው ፍላጎትና ፈቃድ አይመጣም፡፡
ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ። 2ኛ የጴጥሮስ መልእክት 1፡21
ይህ የእስራኤል ዳንሳ በንግግር ውስጥ እስራኤል ዳንሳ እንደዚህ ይላል፡፡
"እስኪ ነቢይ መሆን የምትፈልጉ??_______አንተን ነቢይ ለማድረግ ከጌታ መስማት አይጠበቅብኝም:: በራሴ ወጭ ነቢይ አደርግሃለሁ:: "
እኔ ከፈለግኩ ብቻ እግዚአብሄር ሳይናገረኝ ነቢይ ላደርግህ እችላለሁ ማለት ስህተት ነው፡፡ እግዚአብሄር እንጂ ሰው ሰውን ወደአግልግሎት ሊጣረ አይችልም፡፡ ይህ አባባል አደገኛና ሰዎች ጥሪው ሳይኖራቸው እግዚአብሄር ለዚያ የተለየ አገልግሎት ሳይጠራቸው እንዲገቡበትና ህይወታቸውን እግዚአብሄር በማይፈልጋቸው ቦታ ላይ እንዲያባክኑ የሚያደርግ አሳች ንግግር ነው፡፡
እነዚህም ጌታን ሲያመልኩና ሲጦሙ መንፈስ ቅዱስ፦ በርናባስንና ሳውልን ለጠራኋቸው ሥራ ለዩልኝ አለ። የሐዋርያት ሥራ 13፡2
ኢየሱስ እንኳን በምድር በነበረበት ጊዜ እንደ ሰው ልጅ በእግዚአብሄር አብ ላይ ሙሉ ለሙሉ ይደገፍ ነበር፡፡ ኢየሱስ እንኳን የሰማሁትን አደርጋለሁ እያለ ይናገር ነበር፡፡
እኔ ከራሴ አልተናገርሁምና፤ ነገር ግን የላከኝ አብ እርሱ የምለውን የምናገረውንም ትእዛዝ ሰጠኝ። ስለዚህ እኔ የምናገረውን አብ እንደ ነገረኝ እንዲሁ እናገራለሁ። የዮሐንስ ወንጌል 12፡49-50
እኔ በአባቴ ዘንድ ያየሁትን እናገራለሁ፤ እናንተም ደግሞ በአባታችሁ ዘንድ ያያችሁትን ታደርጋላችሁ። የዮሐንስ ወንጌል 12፡38
እንዲያውም ከጌታ የሰማውምን ከማድረግ ውጭ ኢየሱስ በራሱ ምንም ማድረግ እንደማይችል ይናገር ነበር፡፡
ስለዚህ ኢየሱስ መለሰ እንዲህም አላቸው፦ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም፤ ያ የሚያደርገውን ሁሉ ወልድ ደግሞ ይህን እንዲሁ ያደርጋልና። የዮሐንስ ወንጌል 12፡19
አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #የመንፈስፍሬ #ቅባት #መንፈስቅዱስ #የእግዚአብሔርመንፈስ #መሪ #ቤተመቅደስ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ነቢያት #ነቢይ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

No comments:

Post a Comment