Popular Posts

Tuesday, October 24, 2017

እሳትን የሚያጠፉ አራት ነገሮች

በምድር ላይ የእግዚአብሄርን ፈቃድ በትጋትና በድፍረት ፈፅመን እንድናልፍ ከሚያግዙ ነገሮች አንዱ ግለት እሳትና መቀጣጠል ነው፡፡ ሰው በምድር ላይ የእግዚአብሄርን ፈቃድ የሚፈፅምበት እምቅ ጉልበት ኖሮት እሳቱና ግለቱ ከውስጡ ከጠፋ ለምንም አይጠቅምም፡፡ ሰው የእግዚአብሄርን ፈቃድ ለመፈፀም ረሃቡና ጥማቱ ያስፈልገዋል፡፡ እግዚአብሄር በህይወቱ ያየውን ነገር ለማግኘት ቅናት ይጠይቃል፡፡ ሰው ግን ግድ የለሽና ልቡ ሙትት ያለ ከሆነ የእግዚአብሄን ፈቃድ መፈፀም አይችልም፡፡  
እሳትና ግለት ጉልበትን ይሰጠናል እሳትና መቀጣጠል ቅናት የምድር አስቸጋሪ ሁኔዎችን አልፈን እንድንሄድ ያስችለናል፡፡ ሃሞቱ ከፈሰሰ ግን አንዳች ማድረግ ያቅተናል፡፡
የእግዚአብሄርን ነገር ለመጨበጥ ረሀቡና ጥማቱ ከሌለ በውስጣችን የሚወለድ ብዙ ነገር እያለ የትም መድረስ ያቅተናል፡፡   
እነርሱም፦ ሕዝቅያስ እንዲህ ይላል፦ ይህ ቀን የመከራና የተግሣጽ የዘለፋም ቀን ነው፤ ልጆች የሚወለዱበት ጊዜ ደርሶአል ለመውለድም ኃይል የለም። ኢሳይያስ 37፡3
እግዚአብሄር ለብዙ ነገር አስቦንም እያለ መራመድ ያቅታል፡፡ እግዚአብሄር ከፍ ላለ ነገር ጠርቶን እያለ ጉልበት ያጥራል፡፡
ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ገና እንዳልያዝሁት እቈጥራለሁ፤ ነገር ግን አንድ ነገር አደርጋለሁ፤ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እዘረጋለሁ፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ከፍ ከፍ ያለውን የእግዚአብሔርን መጥራት ዋጋ እንዳገኝ ምልክትን እፈጥናለሁ። ፊልጵስዩስ 3፡13-14
እግዚአብሄር እስራኤልን ሊያስወርስ ያለው ብዙ ምድር እያለ ኢያሱ ግን አረጀ፡፡ ልቡ እንዳረጀበት ሰው አቅሙ ሁሉ እያለውቅ ነገር ግን ምንም ማድረግ የማይችል ሰው የለም፡፡
ኢያሱም ሸመገለ በዕድሜም አረጀ እግዚአብሔርም አለው፦ አንተ ሸመገልህ፥ በዕድሜህም አረጀህ፤ ያልተወረሰች እጅግ ብዙ ምድር ገና ቀርታለች፤ ኢያሱ 13፡1
ካሌብ በሰማኒያ አመቱ ትኩስ ነበር፡፡ ሊወርስ ሊወስድ ሊዋጋ እና ሊወጣ የተዘጋጀ ነበር፡፡
ሙሴም በላከኝ ጊዜ እንደ ነበርሁ፥ ዛሬ ጕልበታም ነኝ፤ ጕልበቴም በዚያን ጊዜ እንደ ነበረ፥ እንዲሁ ዛሬ ለመዋጋት ለመውጣትም ለመግባትም ጉልበቴ ያው ነው። ኢያሱ 14፡11
እግዚአብሄን በሃይል ሲያገለግል የነበረው ታላቁ ነቢይ ኤልያስ አንድ ጊዜ ጉልበት አጠረው፡፡ እግዚአብሄር ሊሰራበት ያለው ብዙ ነገር እያለ ልቡ ተሸነፈ እኔ በቃኝ አለ፡፡
እርሱም አንድ ቀን የሚያህል መንገድ በምድረ በዳ ሄደ፤ መጥቶም ከክትክታ ዛፍ በታች ተቀመጠና፦ ይበቃኛል አሁንም፥ አቤቱ፥ እኔ ከአባቶቼ አልበልጥምና ነፍሴን ውሰድ ብሎ እንዲሞት ለመነ። 1ኛ ነገሥት 19፡4
የእግዚአብሄን ህዝብ ለመባረክ ለበረከት ለመሆን አቅሙ ሁሉ እያለን የምንቆመው እሳታችንን ከውስጣችን ሲጠፋ ብቻ ነው፡፡ እሳታችን ከጠበቅን እርምጃችንንና ፍጥነታችን መጠበቅ እንችላለን፡፡ በምንም ሁኔታ ሊያቆመን አይችልም፡፡ ድፍተራችን ከተመታ ግን ምንም ምክኒያት ሊያስቆመን ይችላል፡፡  
ብዙ ነገሮችን ለጌታ የማድረግ እምቅ ጉልበት እያለን እሳታችንን የሚበላውና ለእግዚአብሄር የመሮጥና ሃሞታችን የሚፈሰው ምን እንደሆነ እንመልከት፡፡  
1.      የሰው የንቀት እይታ
ካለተጠነቀቅን የሰው እይታ እና የሰው አስተያየትን ጉልበታችንን ይበላል፡፡ እንዳንወጣ እንዳንወርስ ጌታ ለጠራን ጥሪ እንዳንዘረጋ ያደርጋል፡፡
ዳዊት የወንድሞቹን ንቀት ቢያምን ኖሮ ታሪክን አይሰራም ነበር፡፡ እኛም በክርስቶስ ያለንበትን ስፍራ ከላየን በስተቀር ምንም ማድረግ የማንችል ከንቱ ሆነን እንቀራለን፡፡
ታላቅ ወንድሙም ኤልያብ ከሰዎች ጋር ሲነጋገር ሰማ፤ የኤልያብም ቍጣ በዳዊት ላይ ነድዶ፦ ለምን ወደዚህ ወረድህ? እነዚያንስ ጥቂቶች በጎች በምድረ በዳ ለማን ተውሃቸው? እኔ ኵራትህንና የልብህን ክፋት አውቃለሁና ሰልፉን ለማየት መጥተሃል አለው። 1ኛ ሳሙኤል 17፡28
ለአንዳንድ ሰው ምንም ብታደርጉ በቂ አይደለም፡፡ አንዳንደ ሰው ምንም ብትሆኑ አይቀበላችሁም፡፡ የሰውን ንቀት ሰምተን ከቆምን ለምንም አንሆንም፡፡
2.     የእግዚአብሄር ቃል እጦት
የእግዚአብሄር ቃል በእምነት እንዴት እንደምንንራመድ ምሳሌዎችን እየጠቀሰ ያስተምረናል ያበረታታናል፡፡ እሳቱን የሚቆሰቁሰው የእግዚአብሄር ቃል ከሌለን እግዚአብሄር በህይወታችን ያየውን ለመውረስ እንዘረጋም፡፡ እግዚአብሄ ለእኛ ያለውን ለማግኘት ካልተዘረጋን ደግሞ አንወርስም፡፡
እንግዲህ ታላቅ ብድራት ያለውን ድፍረታችሁን አትጣሉ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና። ዕብራውያን 10፡25-36
የእግዚአብሄር ቃል ማበረታቻና እሳታቸውን ጠብቀው እግዚአብሄርን ደስ ያሰኙ የቅዱሳን ህይወት ምስክርነት ልባችንን ያቀጣጥለዋል፡፡ 
እንግዲህ እነዚህን የሚያህሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን፥ እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ ቶሎም የሚከበንን ኃጢአት አስወግደን፥ የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና። በነፍሳችሁ ዝላችሁ እንዳትደክሙ፥ ከኃጢአተኞች በደረሰበት እንዲህ ባለ መቃወም የጸናውን አስቡ። ዕብራውያን 12፡1-3
3.     ጭንቀትና የኑሮ ፍርሃት
ሰው ሲፈራ ጉልበቱ ይክደዋል፡፡ ጀግንነት ግን የፍርሃትን ስሜት የማይሰማው ሳይሆን የሚሰማውን የፍርሃት ስሜት ተቀብሎ ከአላማው የማይቆም ሰው ነው፡፡ ድፍረት የፍርሃትን ስሜት አለመስማት አለመቀበል ነው፡፡ የፍርሃት ስሜት ይመጣል ነገር ግን እየፈራንም ቢሆን የእግዚአብሄርን ፈቃድ ካደረግን ፍርሃት እኛን የማስቆም አላማውን መፈፀም ያቅተዋል፡፡
በእሾህም የተዘሩት ሌሎች ናቸው፥ ቃሉን የሰሙት እነዚህ ናቸው፥ የዚህም ዓለም አሳብና የባለጠግነት ማታለል የሌላውም ነገር ምኞት ገብተው ቃሉን ያንቃሉ፥ የማያፈራም ይሆናል። ማርቆስ 4፡18-19
4.     የቅዱሳን ህብረት እጥረት
እርስ በእርሳችን የምንቀጣጠልበት ማቀጣጠያ እሳት በእያንንዳችን ውስጥ አለ፡፡ ስንሰበሰብ የእግዚአብሄርን ነገር ስናወጋ ስንበረታታ እሳታችን ይለኮሳል፡፡ የወንድሞች የፀጋ ቃል ባለንበት እንዳንቆም ከከበበን ነገሮች አልፈን እንድንዘረጋ አቅማችንን ያድሳል፡፡
ለፍቅርና ለመልካምም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ፤ በአንዳንዶችም ዘንድ ልማድ እንደ ሆነው፥ መሰብሰባችንን አንተው እርስ በርሳችን እንመካከር እንጂ፤ ይልቁንም ቀኑ ሲቀርብ እያያችሁ አብልጣችሁ ይህን አድርጉ። ዕብራውያን 10፡24-25
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #እሳት #ህብረት #ቃል #መቀጣጠል #ክብር #አገልግሎት #መዋረድ #መርካት #ፀጋ #እውቀት #ኢየሱስንተመልክተን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ብፅእና #እምነት #ታላቅነት #ማገልገል #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Monday, October 23, 2017

ህይወትን ፍፁም የሚያደርጉ አምስቱ የእግዚአብሄር አቅርቦቶች

በህይወት ለማግኘት የምንፈልገውና እንዲሆንልን የምንጥራቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ህይወት በራሱ ፍፁም አይደለም ጉድለት አለው፡፡ ህይወት በራሱ ፍፁም አይደለም፡፡ ህይወትን ምንም ሳይጎድለው ፍፁም የሚያደርገው የእግዚአብሄር አሰራር ብቻ ነው፡፡
እግዚአብሔር ልቡ በእርሱ ዘንድ ፍጹም የሆነውን ያጸና ዘንድ ዓይኖቹ በምድር ሁሉ ይመለከታሉና። 2ኛ ዜና 16፡9
ህይወትን ፍፁም የሚያደርገው አምስቱ የእግዚአብሄር አሰራሮችን እንመልከት
1.      ስንደክም የሚያበረታን የእግዚአብሄር ሃይል
ሰው በሃይሉ አይበረታም፡፡ ሰው ይደክማል፡፡ ሰው በራሱ መሄድ የሚችለው ትንሽ ነው፡፡ ሰው በራሱ ሃይል ብቻ ከታመነ እግዚአብሄር በህይወቱ ያቀደውን ከፍ ያለ ሃሳብ መፈፀም ይሳነዋል፡፡ ሰው በእግዘአብሄር ሃይል ላይ ከተደገፈ ግን የእግዚአብሄርን ሃሳብ በህይወቱ አገልግሎ ማለፍ ይችላል፡፡
እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ። 2ኛ ቆሮንቶስ 12፡9
2.     ተቀባይነት እንዲኖረው የሚያደርግ የእግዚአብሄር ሞገስ
ሰው በተፈጥሮው ሰውን ለመውደድ ብዙ መመዘኛዎች አሉት፡፡ ሰው ግን ካለምክኒያት እንዲወደን የሚያደርግ የእግዚአብሄር አሰራር ነው፡፡ እግዚአብሄር በህይወታችን ያየው ቦታ እንድንደርስ ሞገስን ይሰጠናል፡፡ ሰዎች ፊታችንን ሲቀበሉና ሃሳባችንን ሲሰሙና ሲቀበሉ ስናይ የእግዚአብሄርን ድንቅ አሰራር እንመለከትበታለን፡፡
እነሆ፥ የማታውቀውን ሕዝብ ትጠራለህ፥ የእስራኤልም ቅዱስ አክብሮሃልና ስለ አምላክህ ስለ እግዚአብሔር የማያውቁህ ሕዝብ ወደ አንተ ይሮጣሉ። ኢሳይያስ 55፡5
በእርሱም ስለ ስሙ በአሕዛብ ሁሉ መካከል ከእምነት የሚነሣ መታዘዝ እንዲገኝ ጸጋንና ሐዋርያነትን ተቀበልን፤ ሮሜ 1፡5
ለአገልግሎቱ ሾሞኝ ታማኝ አድርጎ ስለ ቈጠረኝ፥ ኃይል የሰጠኝን ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታችንን አመሰግናለሁ፤ 1ኛ ጢሞቴዎስ 1፡12
3.     አስተዋይ የሚያደርግ የእግዚአብሄር ጥበብ
የእግዚአብሄርን ፈቃድ በህይወታችን ፈፅመን እግዚአብሄርን በምድር ላይ እንድናከብረው እግዚአብሄር ብርሃንን ይሰጠናል፡፡ እግዚአብሄር ከአስተማሪዎቻችን ይልቅ ጥበበኛ ያደርገናል፡፡ የምናልፈው ከማይመስለን ከባድ ፈተና ሊታደገን እግዚአብሄር መረዳትን በመስጠት መውጫውን ያዘጋጃልናል፡፡ አስበን የማናውቅውን ጥልቀ ነገር መረዳትን ይሰጠናል፡፡ በጥናትና በአእምሮ እውቀት የማይመጣ መገለጥ በህይወታችን ሲመጣ እግዚአብሄር በህይወታችን ሊሰራ ላለው ተልእኮ አስፈላጊ ስለሆነ በቀላሉ ለመረዳት የማይቻለውን የመንፈስን ነገር መረዳትን እናገኛለን፡፡
እግዚአብሔርም ለሰሎሞን እጅግ ብዙ ጥበብና ማስተዋል በባሕርም ዳር እንዳለ አሸዋ የልብ ስፋት ሰጠው። የሰሎሞንም ጥበብ በምሥራቅ ካሉ ሰዎች ሁሉ ጥበብና ከግብጽ ጥበብ ሁሉ በለጠ። 1ኛ ነገሥት 4፡29-30
ከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋል። ያዕቆብ 1፡5
4.     የእግዚአብሄር አቅርቦት

እግዚአብሄር ወደጠራን ጥሪ መግባት እንድንችል ይኖረናለ ብለን የማንገምተውን የገንዘብ አቅርቦት እግዚአብሄር ወደእኛ ሲያመጣ የእግዚአብሄርን አሰራር እናይበታለን፡፡
በተነ፥ ለምስኪኖች ሰጠ፥ ጽድቁ ለዘላለም ይኖራል ተብሎ እንደ ተጻፈ፥ እግዚአብሔር፥ ሁልጊዜ በነገር ሁሉ ብቃትን ሁሉ አግኝታችሁ ለበጎ ሥራ ሁሉ ትበዙ ዘንድ፥ ጸጋን ሁሉ ሊያበዛላችሁ ይችላል። 2ኛ ቆሮንቶስ 9፡8-9
5.     ከሃዘን በላይ የሚያደርገን ሰላምና ደስታ

በምድር ላይ የሚያሳዝኑ ብዙ ነገሮች ይገጥሙናል፡፡ ነገር ግን የሚያሳዝነው ነገር እያለ ከሃዘን በላይ እንድንኖር የሚደርገን የእግዚአብሄር ስጦታ ደስታ ነው፡፡ ሊሰብረን የመጣው ሃዘን እንደፈሳሽ ውሃ ያልፋል፡፡ ሊያስቆመን የመጣው ሃዘን በልባችን ባለው ደስታ ይዋጣል፡፡ ልባችን ሊሰብር የመጣው ሃዘን አቅም ያጣል፡፡
እንግዲህ እናንተ ደግሞ አሁን ታዝናላችሁ፤ ነገር ግን እንደ ገና አያችኋለሁ ልባችሁም ደስ ይለዋል፥ ደስታችሁንም የሚወስድባችሁ የለም። ዮሃንስ 16፡22
በማይነገርና ክብር በሞላበት ሐሤት ደስ ይላችኋል። 1ኛ ጴጥሮስ 1፡8
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#ኢየሱስ #ጌታ #ብልፅግና #የብልፅግናወንጌል  #በረከት #ስኬት #ጥበብ #ማስተዋል #ሞገስ #አቅርቦት #ሃይል #ፀጋ #እረኛእግዚአብሄር #ስምረት #መሰረታዊፍላጎት #ሁሉየእናንተነውና #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #የተትረፈረፈህይወት #መፅሃፍቅዱስ #ሰላም #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ #እወጃ #መናገር #ፅናት #ትግስት #መሪ

Tuesday, October 17, 2017

የእግዚአብሔር እረኛነት የሚገለጥባቸው ሶስት ዋና ዋና ጥቅሞች

አምላክ ያለው ሰው ጥቅሙ ይህ ነው፡፡ እግዚአብሔር እረኛ ነው፡፡ እግዚአብሔር ይመራል ፣ ያበረታል ያፅናናል፡፡ የእግዚአብሔር እረኝነት የሚገለጥባቸው ሶስት ዋና ዋና ነገሮችን እንመልከት
1.      እግዚአብሔር ይመራል
እግዚአብሔር አምላኩ የሆነለት ህዝብ ዋነኛው ጥቅም በእግዚአብሔር ማስተዋል መጠቀም ነው፡፡ እግዚአብሔር ማስተዋል አይመረመርም፡፡ እግዚአብሔር ሁሉን ያውቃል፡፡ ይህ ሁሉን የሚያውቅ እግዚአብሔር መንጋ ከመሆን የተሻለ ምን ነገር አስተማማኝ ነገር ይኖራል፡፡ እግዚአብሔር ይመራናል፡፡ እግዚአብሔር ባለንበት ደረጃ ወርዶ ይናገረናል፡፡ እግዚአብሔር መረዳት በምንችልበት መጠን እና ቋንቋ ሃሳቡን ይገልጥልናል፡፡ እግዚአብሔር ከተናገረ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር እንደተረዳን እርግጠኛ እስኪሆን ድረስ ይናገራል፡፡
እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፥ የሚያሳጣኝም የለም። በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፤ በዕረፍት ውኃ ዘንድ ይመራኛል። ነፍሴን መለሳት፥ ስለ ስሙም በጽድቅ መንገድ መራኝ። መዝሙር 23፡1-3
2.     እግዚአብሔር ያበረታል
እግዚአብሔር ትክክለኛውን አቅጣጫ ማሳየት ብቻ ሳይሆን በዚያ መንገድ እንድንሔድ ሃይልን ይሰጠናል፡፡ እግዚአብሔር ያበረታል፡፡ እግዚአብሔር ይደግፋል፡፡
አላወቅህምን? አልሰማህምን? እግዚአብሔር የዘላለም አምላክ፥ የምድርም ዳርቻ ፈጣሪ ነው፤ አይደክምም፥ አይታክትም፥ ማስተዋሉም አይመረመርም። ለደካማ ኃይልን ይሰጣል፥ ጕልበት ለሌለውም ብርታትን ይጨምራል። ኢሳያስ 40፡28-29
3.     እግዚአብሔር ያፅናናል
እግዚአብሔር ልባችንን ያፅናናል፡፡ በምድር ላይ እኛን ለማሳዘን የሚመጡ ብዙ ነገሮች ቢኖሩም ከሁሉም በላይ እንድንምኖትር እግዚአብሔር ያፅናናል እግዚአብሔር ልባችን በደስታ ይደግፋል፡፡ ከሁኔታ ጋር ያልተያያዘ ደስታን ይሰጠናል፡፡ ከሁኔታዎች ባላይ እንድንኖር ልባችንን ያፅናናል፡፡  
የርህራሔ አባት የመፅናናት ሁሉ አምላክ የሆነው የጌታችን የእየሱስ ክርስቶስ አባትና አምላክ ይባረክ፡፡ 1ኛቆሮንቶስ 13
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ያድርጉ!
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#ኢየሱስ #ጌታ #መሪነት #ያበረታል #ያፅናናል #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #ልብ #እምነት #ምሪት #ድምፅ #ጌታ #ሰላም #ደስታ #አቢይ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Monday, October 16, 2017

እግዚአብሔር ለምን? የሚለው ጥያቄ ግድ ይለዋል

እግዚአብሔር ምን እንደምናደርግ ብቻ ሳይሆን ለምን እንደምናደረገው ምክኒያታችንን ማወቅ ይፈልጋል፡፡ የምንሰራውን ነገር ብቻ ሳይሆን ለምን እንደምንሰራው ግድ ይለዋል፡፡ እግዚአብሔር ንግግራችንን ብቻ ሳይሆን ልባችንንም ይመዝናል፡፡ እግዚአብሔር ድርጊታችንን ብቻ ሳይሆን ለድርጊቱ ያነሳሳንን ነገር ያያል፡፡
አንድን ነገር ስናደርግ በትህትና ይሁን በትእቢት እንዳደረግነው እግዚአብሔር የልባችንን ሃሳብ ይመዝናል፡፡ ስለዚህ ነው ሰዎች ትእቢተኛ ያሉትን ኢየሱስን እግዚአብሔር በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ እርሱ ነው እርሱን ነው እርሱን ስሙት ያለው፡፡ (ማቴዎስ 3፡17) ለዚህም ነው መልካም የመሰለን የሰው ሃሳብ ያመጣው ጴጥሮስ አንተ ሰይጣን ተብሎ በኢየሱስ የተገሰፀው፡፡ (ማቴዎስ 16፡23)
ገንዘባችንን ስንሰጥ ለምን እንደሰጠን አግዚአብሔር ልባችንን ይመዝናል፡፡ ገንዘባቸውን ለታይታ ፣ ሰዎችን ጉድ ለማሰኘትና ከሰው ክብርን ለማግኘት የሚሰጡትን ፈሪሳዊያን ልባቸውን እንዲያጠሩ ኢየሱስ አስተምሮዋልል፡፡
ለሰዎች ትታዩ ዘንድ ምጽዋታችሁን በፊታቸው እንዳታደርጉ ተጠንቀቁ፤ ያለዚያ በሰማያት ባለው አባታችሁ ዘንድ ዋጋ የላችሁም። ማቴዎስ 6፡1
በሰዎች ፊት ቅዱስ ሃሳብ የሚባል ሃይማኖታዊ ነገር እንኳን ስናደርግ እግዚአብሔር ግን ለምን እንዳደረግነው ልባችንን ይመዝናል፡፡
ለሰውም እንዲታዩ ሥራቸውን ሁሉ ያደርጋሉ፤ ስለዚህ አሽንክታባቸውን ያሰፋሉ ዘርፉንም ያስረዝማሉ፥ በምሳም የከበሬታ ስፍራ፥ በምኵራብም የከበሬታ ወንበር፥ በገበያም ሰላምታና፦ መምህር ሆይ መምህር ሆይ ተብለው እንዲጠሩ ይወዳሉ። ማቴዎስ 23፡5-7
ለእግዚአብሔር ብለን የምናደርገውን ነገር እግዚአብሔር ይመዝነዋል፡፡ ለታይታ ወይም በፉክክር ያደረግነው ነገር እግዚአብሔር በእሺታ አይቀበለውም፡፡
የእግዚአብሔርን ፈቃድ እንደሚያደርጉ እንደ ክርስቶስ ባሪያዎች እንጂ ለሰው ደስ እንደምታሰኙ ለታይታ የምትገዙ አትሁኑ። ለሰው ሳይሆን ለጌታ እንደምትገዙ በትጋትና በበጎ ፈቃድ ተገዙ፤ ኤፌሶን 6፡6-7
ምንም ያህል መልካም ነገር ቢሆን በፍቅር ያልተደረገ ነገር ከንቱ ነው ምንም አይጠቅመንም፡፡ ከፍቅር ውጭ ያለ መነሻ ሃሳብ ከንቱ ነው፡፡ በጥላቻ በፉክክር በትእቢት ከማን አንሼ በማለት የተደረገ ምንም መልካም ነገር ፍሬ ቢስ ከንቱ ድካም ነው፡፡
በሰዎችና በመላእክት ልሳን ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮኽ ናስ ወይም እንደሚንሽዋሽዋ ጸናጽል ሆኜአለሁ። ትንቢትም ቢኖረኝ ምሥጢርንም ሁሉና እውቀትን ሁሉ ባውቅ፥ ተራሮችንም እስካፈልስ ድረስ እምነት ሁሉ ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ። ድሆችንም ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል፥ ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም። 1ኛ ቆሮንቶስ 13፡1-3
በመጨረሻም ምን ሰራን ብቻ ሳይሆን ለምን ሰራነው የሚለውም ይፈተናል፡፡ እግዚአብሔር ምን ሰራን ከሚለው ያለነሰ ለምን ሰራነው የሚለው ግድ ይለዋል፡፡
ማንም ግን በዚህ መሠረት ላይ በወርቅ ቢሆን በብርም በከበረ ድንጋይም በእንጨትም በሣርም ወይም በአገዳ ቢያንጽ፥ የእያንዳንዱ ሥራ ይገለጣል፤ በእሳት ስለሚገለጥ ያ ቀን ያሳያልና፥ የእያንዳንዱም ሥራ እንዴት መሆኑን እሳቱ ይፈትነዋል። ማንም በእርሱ ላይ ያነጸው ሥራ ቢጸናለት ደመወዙን ይቀበላል፤ የማንም ሥራ የተቃጠለበት ቢሆን ይጎዳበታል፥ እርሱ ራሱ ግን ይድናል ነገር ግን በእሳት እንደሚድን ይሆናል። 1ኛ ቆሮንቶስ 3፡12-15
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos

#እምነት #ሃሳብ #መነሻሃሳብ #ልብ #ንፁህ #ፍቅር #ፉክክር #ቃል #ክብር #የእግዚአብሔርቃል #ቃሉንመስማት #እወጃ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Sunday, October 15, 2017

ልባችሁን አጥሩ

ወደ እግዚአብሔር ቅረቡ ወደ እናንተም ይቀርባል። እናንተ ኃጢአተኞች፥ እጆቻችሁን አንጹ፤ ሁለት አሳብም ያላችሁ እናንተ፥ ልባችሁን አጥሩ። ያዕቆብ 4፡8
እግዚአብሄር ሲጠራንና የተስፋ ቃል ሲገባልን ሁለት ሃሳቦች በልባችን ይነሳሉ፡፡
አንደኛው እግዚአብሄርን ለማገልገል እድሉን አገኘሁ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ የሚል ሃሳብ ነው፡፡ የእግዚአብሄርን ህዝብ ለማገልገል እግዚአብሄር ታማኝ አደርጎ ስለቆጠረን ደስ ይለናል፡፡ ያለንን ለእግዚአብሄር ህዝብ ማካፈል እንደ እድል እንቆጥረዋለን፡፡ የእግዚአብሄር መጠቀሚያ መሆንንና እግዚአብሄርን ማገልገልን እንደ ትልቅ መብት እናየዋለን፡፡ ሰማይና ምድር የሰራው እግዚአብሄር ሊጠቀምብን
ለአገልግሎቱ ሾሞኝ ታማኝ አድርጎ ስለ ቈጠረኝ፥ ኃይል የሰጠኝን ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታችንን አመሰግናለሁ፤ስለወደደ ልባችን በደስታ ይሞቃል፡፡ 1ኛ ጢሞቴዎስ 1፡12
እግዚአብሄር ሲጠራን በልባችን የሚነሳው ሌላኛው ሃሳብ ደግሞ በቃ አሁን እጠቀማለሁ የሚል ነው፡፡ በጥሪያችን ስም ዝነኛ መሆን ፣ በጥሪያችን ተጠቅመን እግዚአብሄ የሰጠንን ሃይልን ለፈለግነው ነገር ማዋል ፣ ተሰሚነታችንን ተጠቅመን የግል ጥቅማችንን ማሳደድ ፣ እግዚአብሄር ለአገልግሎት የሰጠንን ተቀባይነት ለራሳችን ጥቅም ማዋል ፣ ባለን ጥሪ ተጠቅመን ሀብታም መሆንና  የአግልግሎታችንን ክብር ወደ እኛ ማዞር ሃሳብ ይነሳል፡፡
እግዚአብሄር ታዲያ እንዲህ ይላል ሁለት ሃሳብ ያለችሁ ልባችሁን አጥሩ፡፡ እግዚአብሄር ወደ ጠራን አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ የሚለቀን ልባችንን ስናጠራ ብቻ ነው፡፡
ልባችን ሲጠራ እግዚአብሄርን የምናገለግለው እግዚአብሄር ብቻ ስለሆነ ብቻ ስለሆነ ይሆናል፡፡ እግዚአብሄርን የምናገለግለው የእግዚአብሄርን ህዝብ ለመጥቀም ብቻ ሲይሆናል፡፡ የእግዚአብሄርን ቤት የምንሰራው ለራሳችን ቤትን ለመስራት አይሆንም፡፡ የእግዚአብሄን ህዝብ የምናገለግለው እግዚአብሄር ወደአየላቸው ተራ እንዲደርሱ በቅንነት ለመርዳት እንጂ ኑሮዋችንን ለመስራት አይሆንም፡፡ ልባችንን ስናጠራ እግዚአብሄር ወዳየልን አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ እንለቀቃለን፡፡
ሁለት አሳብም ያላችሁ እናንተ፥ ልባችሁን አጥሩ። ያዕቆብ 4፡8
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር   share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#እምነት #ሃሳብ #መነሻሃሳብ #ልብ #ንፁህ #ማየት #አለማየት #ቃል #የእምነትተጋድሎ #የእግዚአብሄርቃል #ቃሉንመስማት #እወጃ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ

Saturday, October 14, 2017

ፈትኑኝ፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር

በዚህ ፈትኑኝ፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፡፡ ሚልክያስ 3፡10
እግዚአብሄር እውነተኛ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሄር መልኩ አንድና አንድ ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሄር አይለወጥም፡፡ እግዚአብሄር አይዋሽም፡፡ እግዚአብሄር ታላቅ ነው፡፡ እግዚአብሄር የሚፈራው የለም፡፡ እግዚአብሄ ቅዱስ ነው፡ሸ እግዚአብሄ ንፁህ ነው፡፡ እግዚአብሄር ሊደብቀው የሚፈልገው ነገር የለም፡፡ እግዚአብሄር አውነትን ይናገራል፡፡
የእግዚአብሄ ቃል እውነት ነው፡፡ የእግዚአብሄር ቃል የተፈተነ ነው፡፡ የእግዚአብሄ ቃል ተፈትኖ ያለፈ አስተማማኝ ማነም ሰው ሊደገፍበት የሚችል ነው፡፡  
በምድር ላይ እንደ ተፈተነ ሰባት ጊዜ እንደ ተጣራ ብር የእግዚአብሔር ቃላት የነጹ ቃላት ናቸው። መዝሙር 12፡6
ስለዚህ ነው እግዚአብሄር ፈትኑኝ የሚለው፡፡ ስለዚህ ነው እግዚአብሄር ያልፈፀምኩት ቃል የት አለ? ኑና እንዋቀስ የሚለው፡፡ እግዚአብሄ ቃሉን ሁልጊዜ ስለሚጠብቅ ከማንም ጋር ለመዋቀስ አይፈራም፡፡ እግዚአብሄር ቃሉን ሙሉ ለሙሉ ስለሚጠብቅ ኑና እንዋቀስ ይላል፡፡ እግዚአብሄር የማንም ባለእዳ አይደለም፡፡
ኑና እንዋቀስ ይላል እግዚአብሔር፤ ኃጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች፤ እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ ትጠራለች። ኢሳያስ 1፡18
እግዚአብሄር መጠየቅን አይፈራም፡፡ እግዚአብሄር በቃሉ መፈተንን ይወደዋል፡፡ እግዚአብሄር እውነተኛ ስለሆነ ሁልጊዜ በቃሉ እንድንፈትነው ይጋብዘናል፡፡
በዚህ ፈትኑኝ፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፡፡ ሚልክያስ 3፡10
ይህን ፅሁፍ ለሌሎች ሼር share ማድረግ ቢወዱ
ለተጨማሪ ፅሁፎች https://www.facebook.com/abiy.wakuma/notes
ለቪዲዮ መልእክቶች https://www.youtube.com/user/awordm/videos
#እምነት #ማየት #አለማየት #ቃል #የእምነትተጋድሎ #የእግዚአብሄርቃል #ቃሉንመስማት #እወጃ #ቤተክርስትያን #አማርኛ #ስብከት #መዳን #መፅሃፍቅዱስ #መንፈስቅዱስ #ህይወት #ፌስቡክ #አቢይዋቁማ #አቢይዋቁማዲንሳ