Popular Posts

Monday, May 30, 2016

ዘፈን ሐጢያት ነውን!?

ክርስትና ስር ነቀል የህይወት ለውጥ ነው፡፡ ክርስትና ጌታን መከተል ነው፡፡ ክርስትና ጌታ በቃሉ ያዘዘንን መፈፀም ነው፡፡ ጌታ በቃሉ የከለከለውን አለማድረግ ነው፡፡
ከሰሞኑ ዘፈን ሃጢያት ነው? አይደለም? የሚሉ ክርክሮች ሰምተናል፡፡ ዘፈን ሃጢያትነቱ ምኑ ላይ ነው? የሚለው ጥያቄ መነሳቱ ስለዘፈን ያለንን ግንዛቤ እንድንፈትሽ እንደ መልካም አጋጣሚ ልንመለከተው እንጂ ልንረበሽበት አይገባም፡፡ ከዚህም በኋላ የምናምነውን ለምን እንደምናምነው ሊፈትሹ የተለያዩ ሃሳቦች ሊነሱ ይችላሉ፡፡ ከእኛ የሚጠበቀው የምናምነውን ለምን እንደምናምነው ከቃሉ አጥንቶ በቃሉ ላይ መቆም ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ እኔም በልቤ ያለውን ለማካፈል ወደድኩ፡፡
እንዳንዳንድ ሰዎች "ሃጢያት ነው ሃጢያት ነው በቃ" በማለት መልስ መልሰዋል፡፡ እንደሚሉት ዝግት አርጌ ያለምክኒያት ማሳመን የዚህ ፅሁፍ ፀሃፊ አላማ አይደለም፡፡ ምክኒያቱም እግዚአብሄር አንድን ነገር ሲከለክል ሙሉ ምክኒያት አለው፡፡ እግዚአብሄር አንድን ትእዛዝ ሲሰጠን የዚያ ትእዛዝ ትክክለኛውን መንፈሱን ወይም ዋና አላማውን መገንዘን ለምን እንደተከለከለ ጠንቅቀን እንድናውቅና ምኑ እንደተከለከለ ተረድተን እንድንጠነቀቅ ይረዳናል፡፡ ለዚህም ነው ቃሉ የእግዚአብሄር ቃል በሙላት ይኑርባችሁ በማለት የሚያዘው፡፡ 
እውነት ነው  እግዚአብሄር ሁሌ "ይህንን ያዘዝኩበት ምክኒያት ይሄ ነው" ብሎ ላያስረዳን ይችላል፡፡ አንዳንዱን ባይገባንም እንቀበለውና በየዋህነት እንታዘዛለን የተከለከልነውንም አናደርግም፡፡ እግዚአብሄር በቃሉ ይህን አታድርግ ሲለን ለምን እንደከለከለ ባይገባንም እንኳን የምንታዘዘው ነገር ይኖራል፡፡ በመታዘዛችን እንድናለን እንጂ በፍፁም አንጎዳም፡፡ ባለመታዘዝ ግን አደጋ ላይ ልንወድቅ እንወድቃለን፡፡
ለምሳሌ ዘፈን ለምን ሃጢያት ሆነ ወይም እግዚአብሄር የዘፈንን ምኑን እንደጠላው ማወቅ በደስታና በእውቀት እንድንታዘዘው እንዲሁም ሌሎች ለሚጠይቁን መልስ መስጠት የተዘጋጀን እንድንሆን ያስታጥቀናል፡፡
ዘፈንን በተመለከተ ለምን እግዚአብሄር በቃሉ እንደከለከለ ከተረዳን ዘፈን የቱ ነው? ዘፈን የቱ አይደለም? የሚሉ ጥያቄዎች እንድንመልስና ራሳችንን ከተከከለው ነገር በትጋት እንድንጠብቅ ይረዳናል፡፡
በአጠቃላይ ግን … ዓለምም በሞላው በክፉው እንደ ተያዘ እናውቃለን።1ኛ ዮሃንስ 5፡19 እንደሚል አለም በክፉ ስለተያዘና ዳግመኛ ካልተወለዱ አለማዊ ሰዎች የሚወጣው ማንኛውም የህይወት መርህ አለማዊነትን የሚያስፋፋ እንጂ ወደ እግዚአብሄር የሚያመራ ሊሆን እንደማይችል መገመት አይከብድም፡፡ በእግዚአብሄር ቃል የማይለካና ከእግዚአብሄር ቃል ጋር መሄዱና አለመሄዱ ከእግዚአብሄር ቃል ጋር መጋጨቱና አለመጋጨቱ የማይፈተሽ አስተሳሰብም ሆነ የህይወት መርህ ወደ እግዚአብሄር በፍፁም አያመለክትም፡፡ ለክብሩ ወደ ፈጠረንንና ለእርሱ መገዛትና ለእርሱ ብቻ ልንኖርለት ወደሚገባን ወደ  እግዚአብሄር አለማሳየቱ ብቻ ሳይሆን እንዲያውም ከእግዚአብሄር ሊያርቀንና ይህንን ፍልስፍና የተከተሉትን ሰዎች ሁሉ ወደ ዘላለም ጥፋት የሚመራ ከሆነ ዘፈን ነው፡፡
የማይታየው ባሕርይ እርሱም የዘላለም ኃይሉ ደግሞም አምላክነቱ ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ ከተሠሩት ታውቆ ግልጥ ሆኖ ይታያልና፤ ስለዚህም እግዚአብሔርን እያወቁ እንደ እግዚአብሔርነቱ መጠን ስላላከበሩትና ስላላመሰገኑት የሚያመካኙት አጡ፤ ነገር ግን በአሳባቸው ከንቱ ሆኑ የማያስተውለውም ልባቸው ጨለመ። ሮሜ 1፡20-21
ይህንን ለመመልከት ዘፈን ምን እንደሆነ እይታዬን ልሰንዝር
1.       ዘፈን የእግዚአብሄርን ቃል ያላማከለ በሃጢያት የወደቀው የሰው አስተሳሰብ ነው፡፡ ዘፈን ለራሳቸው የራሳቸው ጌታ በሆኑ ሰዎች የሚዘፈን እየሱስን የህይወታቸው ጌታ ያላደረጉ ሰዎች የሚዘፍኑት እንዲያውን በተዘዋዋሪ በሰይጣን የሚሽከረከሩ ሰዎች የሚፃፍና የሚንጎራጎር ነው፡፡
በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው ኤፌሶን 2፡1
2.      እዚህ ጋር ከቃሉ ውጭ ወጥተሃል ተብሎ የሚነገር አይደለም፡፡ ዘፈን  ስለፍቅር ስለሰው ስለደስታ ፍልስፍና ነፀብራቅ የሆነ፡፡
እንደ ክርስቶስ ትምህርት ሳይሆን፥ እንደ ሰው ወግና እንደ ዓለማዊ እንደ መጀመሪያ ትምህርት ባለ በፍልስፍና በከንቱም መታለል ማንም እንዳይማርካችሁ ተጠበቁ። ቆላሲያስ 2፡8
3.      ዘፈን ሰውን ያማከለ ሲሆን አብዛኛው ሰው የትኛውን ይወደዋል? የቱ ያስደስተዋል? ተብሎ በሰው ደስታ ላይ ያማከለና ሰውን ለመሳብ የሚደረስ ድርሰት 
4.      ዘፈን እንዲሸጥ የሰውን ስጋዊ ፍላጎት የሚያነሳሳ በጊዜያዊ ደስታ ላይ ያተኮረ መፅሃፍ ቅዱስ   "የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለ ገንዘብም መመካት" 1ኛ ዮሃንስ 2፡16 መርህ የሚያስፋፋ
5.      ዘፈን ሰው እግዚአብሄርን እንዲፈራ ምንም የሚያበረክተው አስተዋፅኦ የሌለ ነው
6.     ዘፈን ሰው የስጋዊ ፍላጎቱን ገደብ እንዲያደርግበት ወይም ስጋዊ ፍላጎቱን እንዲቆጣጠር ምንም የሚያደርገው አስተዋፅኦ የሌለ
7.      ዘፈን ሰው እግዚአብሄርን እንዲፈራ የሰማያዊውን አለም እንዲያስብ የማያበረታታውና ጌታን ስለመከተል የሚያበረክተው ምንም ነገር የሌለ
8.      ዘፈን የሚፃፈው የእግዚአብሄርን ፈቃድ ስለማያደርጉ ይልቁንም የስጋቸውንና የልቦናቸውን ፈቃድ ስለሚያደርጉ ሰዎች የህይወት መርህና ልምድ በመሆኑ 
"የሥጋችንንና የልቡናችንን ፈቃድ እያደረግን፥ በሥጋችን ምኞት በፊት እንኖር ነበርን" ኤፌሶን 2፡2
9.     እግዚአብሄር የሰው ልጆች ፈጣሪና ባለቤት ሆኖ የህይወታችን እስትንፋስን የሚሰጠን ሆኖ ሳለ እግዚአብሄርን የእይታ በፍፁም የሚያጠፋ ለእግዚአብሄር የሚገባውን እውቅና የማይሰጥ ነገር ሁሉ ዘፈን ነው፡፡
እነዚህንና እነዚህን የመሳሰሉ መመዘኛዎች የሚያሟላ ማንኛውም ነገር ዘፈን ነው፡፡ እግዚአብሄርን የከለከለው ይህንን ነው፡፡
የዘፈንን ባህሪዎች ስንመለከት ዘፈን ከየት እንደሚመነጭ ምንጩን ካወቅንና የዘፈንን አላማ ከተረዳን ዘፈን ሃጢያት መሆኑን በፍፁም ልንጠራጠር አንችልም፡፡


https://www.facebook.com/abiy.wakuma

No comments:

Post a Comment