Popular Posts

Wednesday, September 9, 2026

እውነተኛው የዘመን አቆጣጠር



ይህ ወር የወሮች መጀመሪያ፤ የዓመቱም መጀመሪያ ወር ይሁናችሁ። ኦሪት ዘጸአት 12:2

እውነተኛው አዲስ አመት የሚባለው ቃሉን ሰምተን ነጻ የምንወጣበትን ጊዜ ነው። እውነተኛው ዘመን መለወጫ የሚባለው ቃሉን ሰምተን በቃሉ የዳንንበት ቀን ነው።

ዘጸአት ምዕራፍ 12 በአጠቃላይ እግዚአብሔር ለእስራኤል ከግብፅ ነፃ በወጡበት ወቅት አዲስ ጅምር ያደረገበት ምዕራፍ ነው።

ዘጸአት 12፡2 — እግዚአብሔር ለሙሴና ለአሮን እንዲህ አላቸው፦ «ይህ ወር ለእናንተ የወሮች መጀመሪያ፣ የዓመቱም የመጀመሪያ ወር ይሁንላችሁ።»

እስራኤላዊያን ሊያድናቸው የመጣውን የእግዚአብሄር ቃል ሰምተው ከግብጽ ባርነት ነጻ የወጡበትን ቀን የወሩ መጀመሪያ ወሩን ደግሞ የአመቱ መጀምሪያ እንዲሆን ተነገራቸው።

ቀናቸውን እና ወራቸውን አንድ ብለው የጀመሩት ከነጻነታቸው ቀን ጀምረው ነው።

ዘጸአት 13፡3–4 ደግሞ ይህንን አዲስ ቀን እና አዲስ ወር ከግብፅ ነፃ ከመውጣታቸው ጋር ይገናኛል።

በመጽሐፍ ቅዱስ እይታ፣ «አዲሱ ዓመት» የሚቀርበው እንደ ቀላል የቀን መቁጠሪያ ለውጥ ብቻ ሳይሆን፣ በእግዚአብሔር ቤዛነትና ነፃ ማውጣት የተፈጠረ አዲስ ጅምር እንደሆነ ነው።

ዛሬም እውነተኛ ነጻነት የእግዚአብሄርን ቃል ሰምተን ነጻ የምንወጣበት ነጻነት ነው።

ኢየሱስም ያመኑትን አይሁድ፦ እናንተ በቃሌ ብትኖሩ በእውነት ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ፤ እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው። የዮሃንስ ወንጌል 8፡31፣ 32

አዲስ ዘመንም የእግዚአብሄርን ቃል ሰምተን ነጻ የወጣንበትን ቀን ነው።

እውነተኛው ዘመን መለወጫ ደግሞ የዘመን መቁጠሪያ ካላንደር ሳይሆን በእግዚአብሄር ቃል ነጻ የምትወጡበት ቀን ነው።

ነገር ግን ነጻ የሚያወጣውን ፍጹሙን ሕግ ተመልክቶ የሚጸናበት፥ የያዕቆብ መልእክት 1:25

በቃሉ ነጻ ለወጣ ሰው ጷጉሜ 5 የዘመን መለዋጫ ነው። የእግዚአብሄርን ቃል ሰምቶ ነጻ ለማይወጣበት ሰው ግን በመስከረም 1 እንኳን ዘመኑን አይለወጥም።

ስለዚህ ጥያቄው የእግዚአብሄርን ቃል በመስማት እና በማድረግ ዘመናችሁን ለመለወጥ ተዘጋጅታችኋል ወይስ ዘመኑ በራሱ ህይወቴን ይለወጣል ብላችሁ በከንቱ ተስፋ እያደረጋችሁ ነው ?

ህይወትን የሚለወጥ የእግዚአብሁሄር ቃል ብቻ ነው። ቀን ያው የተለመደው ተመሳሳይ ሰኞ ማክሰኞ ሮብ ሃሙስ አርብ ቅዳሜ እሁድ ነው። የእግዚአብሄር ቃል ህይወታችንን ካልለወጠ ቀን ህይወትን ሊለውጥ አይችልም።

አዲስ አመት ህይወታችን በእግዚአብሄር ቃል እንዲለወጥ የመንፈቅድበት አዲስ እድል እንጂ በራሱ የህይወት ለወጥ አይደለም።

መልካም አዲስ አመት መልካም አዲስ ህይወት

አቢይ ዋቁማ ዲንሳ Abiy Wakuma Dinsa

No comments:

Post a Comment